| በአዲስ አበባ የዋጋ ንረት የሚቆጣጠረው... |
|
|
| Wednesday, 26 March 2008 | |
![]() አቶ ሙሉጌታ አሰፋ የዳቦ መጠን ቁጥጥር ይጀመራል በአዲስ አበባ የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠርና ያለአግባብ ትርፍ የሚሰበሰቡ ነጋዴዎችን ለመቆጣጠር የተቋቋመው ግብረ ኃይል ዛሬ ሥራውን ይጀምራል፡፡ በዳቦ ዋጋና መጠን ላይ ዋጋ ለማውጣት ለኢትዮጵያ የጥራትና ደረጃዎች መዳቢ ባለሥልጣን ሀሳብ ያቀርባል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ የንግድ ምዝገባ ፈቃድ ክትትልና ቁጥጥር መምሪያ ኃላፊ አቶ ሙሉጌታ አሰፋ ለሪፖርተር ጋዜጣ እንደገለፁት በአዲስ አበባ አሥሩም ክፍለ ከተሞች ዛሬ ሥራ የሚጀምረው ግብረ ኃይል ከአዲስ አበባ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ፣ ከፖሊስ ኮሚሽን፣ ከማስታወቂያ ቢሮ፣ ከገቢዎች ኤጀንሲ፣ ከግብርና መምሪያ፣ ከየክፍለ ከተሞች የንግድና ኢንዱስትሪ ፅህፈት ቤት ኃላፊዎችና ከአዲስ አበባ የደንብ ማስከበር አገልግሎትን ያካተተ ሲሆን በአሥሩም ክፍለ ከተሞች በተመሳሳይ ኮሚቴው ተቋቁሟል፡፡ ኮሚቴው ሥራውን ሲጀምር እስከ ቀበሌ ድረስ በተዋረድ ለተቋቋመ ኮሚቴ መመሪያ ይሰጣል፡፡ በመመሪያው መሠረት እያንዳንዱ ነጋዴ በሚሸጠው ሸቀጥ ወይም እቃ ዋጋ በግልፅ በሚታይ ቦታ ይለጥፋል፡፡ መመሪያውን ተግባራዊ በማያደርጉት ላይ አስተዳደራዊና ህጋዊ ርምጃ ይወስዳል፡፡ አስተዳደራዊ የተባለው ርምጃ ጥፋተኛ ሆኖ የተገኘን ነጋዴ የንግድ ፈቃድ ሰርዞ የንግድ ቤቱን የኪራይ ውል እስከማቋረጥ እንደሚደርስ ኃላፊው ገልፀዋል፡፡ ህጋዊ ርምጃው ደግሞ በህግ በተደነገገው መሠረት በወንጀል የሚያስከስስ ይሆናል፡፡ "ይህ ሁሉ የሚደረገው ተገቢ ባልሆነ መንገድ ትርፍ ለማግኘት በማሰብ ህብረተሰቡን የሚጐዱ ስግብግብ ነጋዴዎችን ለመቆጣጠር ነው" ያሉት አቶ ሙሉጌታ "ንግድ ትርፍ ካላስገኘ የበጐ አድራጐት ድርጅት ቢመስልም በህገወጥ መንገድ ትርፍ ማግበስበስ ህግ ባለባት ሀገር አይቻልም" ብለዋል፡፡ ህገ ወጥ ንግድ የዋጋ ንረቱን ለማስተካከል እስከቀበሌ በተቋቋመው የቁጥጥር ሰንሰለት አጋጣሚውን በመጠቀም ሙስና ይስፋፋል የሚል ፍርሃት ስለመኖሩ ለተጠየቁት "አብዛኛውን ህዝብ ኑሮ ውድነትና የዋጋ ንረት እየጐዳው ባለበት ሁኔታ ራስን ለመጥቀም ከህገወጦች ጋር የመተባበር ነገር ይኖራል ተብሎ አይገመትም" በማለት አቶ ሙሉጌታ መልስ ሰጥተዋል፡፡ የዋጋ ንረቱን ለመቆጣጠር የወጡ "የህዝብ ማስታወቂያዎች" የሚተገብሯቸው ንፁህ ህሊናና ቀና አመለካከት እንደሚሹ ኃላፊው አልሸሸጉም፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ጥፋት የሚፈፅሙ ከተገኙ ለሌላው ትምህርት የሚሆን ሕጋዊ ርምጃ እንደሚወስድባቸው፣ ለዚህም ቅድመ ዝግጅትና የተቆጣጣሪዎች ሌላ ተቆጣጣሪ መኖሩንም ኃላፊው አመልክተዋል፡፡ "ዋጋ መጨመር ብቻ ሳይሆን ዋጋ መቀነስም ወንጀል ነው" ያሉት አቶ ሙሉጌታ ዋጋ በመቀነስ ሌሎች አነስተኛ ነጋዴዎችን ከጨዋታ ማስወጣት፣ ሞኖፖሊን ይጋብዛልና ተቀባይነት የለውም፡፡ በዳቦ ላይ ቁጥጥር ለማድረግ ይችል ዘንድ የደረጃዎች መዳቢ ባለሥልጣን አንድ ኪሎ ዱቄት ምን ያህል ዳቦ እንደማወጣው ካሰላ በኋላ ጥናቱን ሲያቀርብ እንደሚወስን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ገልፀዋል፡፡ የጥራትና ደረጃዎች መዳቢ ባለሥልጣን ዋጋውንና የግራሙን መጠን ካሳወቀ በኋላ ዳቦ ቤቶች በተቀመጠው ዋጋ መሰረት ግራሙን ሳያጭበረብሩ እንዲሸጡ እንደሚደረግ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአሰግድ ተፈራ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |