|
Wednesday, 26 March 2008 |
 የኦህዴድ 18ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ጋር በተያያዘ በትላንትናው ዕለት በአዳማ (ናዝሬት) የኦሮሞ ጀግኖች ሰማዕታት ሐውልት፣ የክልሉ መገናኛ ብዙሃን ኤጀንሲ ሕንፃ እና የራዲዮ ጣቢያ በይፋ ተመርቆ ተከፍቷል፡፡
ሐውልቱ ከጉልበት እስከ መቀመጫ ድረስ ያለውን አጥንት የሚያሳይ ሲሆን አጥንቱ ረዥም የሰውነት ክፍል የሚወክል፣ ረዥም ጊዜ መራራ ትግል መካሄዱን የሚያመለክት ነው፡፡ የሐውልቱ ጭንቅላት የተያያዘው አንድነትና አብሮ መቆምን ለማሳየት ታስቦ ነው ተብሏል፡፡
የሐውልቱ ግንባታ ብቻ 63.3 ሚሊየን ብር የፈጀ ሲሆን ከዚህ ገንዘብ ውስጥ 23 ሚሊዮን ብር ያህሉን የመከላከያ ሠራዊት አባላት የሆኑ የኦህዴድ የቀድሞ ታጋዮች የተዋጣ ሲሆን ቀሪው በሼህ መሐመድ ሁሴን አልአሙዲ መሸፈኑ፣ ግንባታውንም ሚድሮክ ኮንስትራክሽን ማከናወኑ ታውቋል፡፡
በምረቃው ሥነስርዓት ላይ የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፣ ም/ጠቅላይ ሚኒስትርና የግብርናና ገጠር ልማት ሚኒስትር አቶ አዲሡ ለገሰን ጨምሮ የክልል ባለሥልጣናት፣ ዲፕሎማቶችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
|