| አንድ ቦቴ ውሃ ከ700 እስከ... |
|
|
| Wednesday, 02 April 2008 | |
|
አንድ ቦቴ ውሃ ከ700 እስከ 800 ብር መሸጡ ተደረሰበት
የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት ባለስልጣን ሰሞኑን ባደረገው አሰሳ በአዲስ አበባ ከተማ አንዳንድ አካባቢ አንድ ቦቴ ውሃ ከሰባት መቶ እስከ ስምንት መቶ ብር የሚሸጡ ግለሰቦች መኖራቸውን የባለስልጣኑ የቢዝነስ ዴቨሎፕመንት ምክትል ዋና ሥራ አስከያጅ አቶ ሰኢድ ይመር ለሪፖርተር ጋዜጣ አስታወቁ፡፡ እንደ አቶ ሰኢድ ገለፃ በከተማ ውስጥ የተከሰተው የውሃ ችግርን በመጠቀም የውሃ ቧንቧ መስመር መዝጊያና መክፈቻ (ጌት ቫልቭ) ይዘው የሚቆልፉና የሚከፍቱ እንዳሉ ታወቋል፡፡ በዚህም የባለስልጣኑን የውሃ ስርጭት እንዲዛባ አድርገዋል፡፡ አቶ ሰኢድ አንዳንድ ህገወጥ ግለሰቦች ጌት ቫልቭ በመክፈትና በመዝጋት በኮንቴነር፣ በቦቴ ውሃ በማጠራቀም ሽያጭ እንደሚያካሂዱ አስታውቀዋል፡፡ ምክትል ሥራ አስኪያጁ ከቦታ አቀማመጥ አንፃር ውሃ ወደ ከፍተኛ ቦታ እንዳይሄድ የሚያደርጉ መኖራቸውን ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ማረጋገጡን አስታውቀዋል፡፡ አቶ ሰኢድ በአንዳንድ ቦታ የእሳት አደጋን ለመከላከል የአደጋ ጊዜ የውሃ ማሰራጫ መስመሮች ላይ የውሃ እጥረት አለመኖሩን ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች አገልግሎት የህዝብ ግንኙነትና የግንዛቤ ማስፋፊያ ተወካይ አቶ ከበደ ለገሰ በበኩላቸው በአንዳንድ ቦታዎች ላይ የውሃ እጥረት መኖሩንና ለእሳት አደጋ መጠባበቂያ የውሃ ማሰራጫ መስመሮች ላይ በመንገድ ሥራ ምክንያት የውሃ ስርጭት ችግር እንዳለ ጠቁመዋል፡፡ "ይህ ማለት ግን አሳሳቢ አይደለም" ሲሉ አማራጭ መስመሮች መኖራቸውን አስታውቀዋል፡፡ በሌላ ዜና ቦሌ የሚገኘው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት መኖሪያ አፓርትመንት ውስጥ የውሃ አገልግሎት መቋረጡ ታውቋል፡፡ በአፓርትመንቱ ውስጥ የሚኖሩ የፓርላማ አባላት በህንፃው ውስጥ ውሃ አገልግሎት በመቋረጡ መቸገራቸውን አስታወቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ኅብረት አባል የሆኑት አቶ ወንድሙ ፍስሃ "ውሃ ከተቋረጠ ከአስር ቀን በላይ በመሆኑ በጀሪካን ለማመላለስ ተገደናል" ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ችግሩ እንዲስተካከል ለፓርላማ የአገልግሎት ሰጪ ክፍል ማመልከታቸውን ነገር ግን መፍትሄ አለማግኘታቸውን አቶ ወንድሙ ገልፀዋል፡፡ የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ለገሰ ቢራቱ በህንጻው ውስጥ ውሃ ከተቋረጠ ከአስር ቀናት በላይ መሆኑን ጠቅሰው "በአፓርታማው ውስጥ ያሉ ከሦስት መቶ በላይ የፓርላማ ተወካዮች ከነቤተሰቦቻቸው ተቸግረዋል" ብለዋል፡፡ ችግሩ እንዲፈታ ሪፖርት ማድረጋቸውንና መፍትሄ አለማግኘታቸውን አቶ ለገሰ ገልጸዋል፡፡ የፓርላማ አባላቱን አቤቱታ በተመለከተ አቶ ሰዒድ ይመር "ችግሩ ስለመከሰቱ የገለፀልን አካል የለም" ሲሉ መልስ ሰጥተዋል፡፡ በተሾመ ንቁ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |