| ሰባት አዳዲስ መንገዶችን ለመገንባት... |
|
|
| Wednesday, 02 April 2008 | |
|
ሰባት አዳዲስ መንገዶችን ለመገንባት ለአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች ጥሪ ቀረበ
የመስቀል አደባባይ ቦሌ መንገድ አንዱ ነው ከኢትዮጵያን ሚሌኒየም ክብረ በዓል ጋር ተያይዞ እንዲዘገይ ተደርጐ የነበረው ከመስቀል አደባባይ ቦሌ የሚደርሰውና ሦስት ተላላፊዎችን ያካተተው የመንገድ ሥራና ሌሎች የስድስት አዳዲስ መንገዶች ሥራ በአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች እንዲሠሩ ጥሪ ቀረበ፡፡ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ፍቃዱ ኃይሌ ለሪፖርተር እንደገለፁት በቀጣዩ ሁለት ወራት ውስጥ የሰባቱ መንገዶች ጨረታ ውጤት ይፋ እንደሚሆንና ከእነዚህ ውስጥም ለየት ባለ መልኩ የሚገነባውና ከመስቀል አደባባይ ቦሌ ድረስ ያለው መንገድ አንዱ ነው፡፡ መንገዱ ውስጥ ለውስጥና ከላይ የሚገነቡ ተሻጋሪ መንገዶችን የሚያካት ነው፡፡ ተላላፊ መንገዶቹም ደንበል ህንፃ አካባቢ ወሎ ሠፈር እና ከሚኪሊላንድ መንገድ ወደ ሩዋንዳ በሚወስደው መንገድ ላይ የሚሠሩ ናቸው፡፡ የዚህ መንገድ ግንባታ እንዲጀመር ታቅዶ የነበረው ባለፈው ዓመት እንደነበር ያስታወሱት አቶ ፈቃዱ ለሚሊኒየም ክብረ በዓል ወደ አገር ውስጥ ለሚመጡ እንግዶች የኮንስትራክሽን ግንባታው ችግር እንዳይፈጠር ታስቦ ነው፡፡ አሁን ግን መንገዱን ለማስጀመር የሚቻል በመሆኑ ሥራው ይጀመራል፡፡ በአርባ ሜትር ስፋት በሚገነባው በዚህ መንገድ ግንባታ ምክንያት በአካባቢው ብዙ የሚፈርሱ ቤቶች አለመኖራቸው ታውቋል፡፡ ጠቅላላ የኮንስትራክሽን ሥራው በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን በዚህ መንገድ የሚፈጠር የትራፊክ መጨናነቆችን ያስቀራል ተብሎ ታምኗል፡፡ በተለይ መንገዱ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ለሚመጡ እንግዶች ተብሎ የሚዘጉ መንገዶችን የሚያስቀርና በዚህ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ተሽከርካሪዎች እንዳይስተጓጎሉም ያደርጋል፡፡ ይህንን መንገድ ለመገንባት ቀደም ብሎ በተገመተ ወጪ እስከ 2ዐዐ ሚሊዮን ብር ይፈጃል የተባለ ሲሆን አሁን ባለው ደረጃ ግን ዋጋው ከዚህ ሊጨምር ይችላል፡፡ ከዚህ መንገድ ሌላ የበጀት ዓመቱ ከመጠናቀቁ በፊት 6 የሚሆኑ መንገዶችም በተመሳሳይ መልኩ ሥራዎቻቸው ለኮንትራክተሮች ይሰጣል፡፡ እነዚህ ስድስት መንገዶችም ከአየር ጤና - ታጠቅ አምቦ፣ ከጉርድ ሾላ፣ ሰሚት - የካቦሌ፣ አለምባንክ - የሺደበሌ ሰፈር፣ ከመካኒሳ አደባባይ - ብስራተ ገብርኤል አደባባይ፣ ከአስኮ ዊንጌት - ቀለበት መንገድ እና ከመገናኛ አያት ድረስ ያሉት መንገዶች ናቸው፡፡ የእነዚህ መንገዶች ሥራ የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች እንዲሠሩ የሚፈለግ ሲሆን እስከመጪው ግንቦት ድረስ እያንዳንዱ መንገድ በየትኛው ኮንትራክተር እንደሚሠሩ ይፋ ይደረጋል ተብሏል፡፡ በዳዊት ታዬ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |