| ንዋየ ቅድሳትና ቅርሳ ቅርሶች ወደ... |
|
|
| Wednesday, 16 April 2008 | |
|
ንዋየ ቅድሳትና ቅርሳ ቅርሶች ወደ አውስትራሊያ ሊላክ ሲል ተያዘ
አንድ 20 ፊት ኮንቴነር ሙሉ የቤተክርስቲያን ንዋየ ቅድሳትና ባህላዊ እቃዎች በጅቡቲ በኩል ወደ አውስትራሊያ ሊላክ ሲል ጋላፊ ኬላ ላይ መያዙን የሰሜን ምስራቅ ቀጠና ጉምሩክ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታሁን ቱጂ አስታወቁ፡፡ አቶ ጌታሁን ለሪፖርተር ጋዜጣ እንዳስታወቁት በርካታ የብር መስቀሎች፣ ጸናጽል፣ ማጠንት፣ የቤተክርስቲያን አልባሳት እንዲሁም ከእንጨት የተሰራ እንስራ፣ ጋን፣ ባሕላዊ ወንበሮችና መሰል የቅርስ እቃዎች ወደ አውስትራሊያ ሲላክ መጋቢት 20 ቀን 2000 ዓ.ም በኬላው የፍተሻ ሠራተኞች ተይዟል፡፡ በኃላፊው ገለፃ መሠረት እንዲህ አይነት የቅርስ እቃዎች በኬላው በኩል ወደ ውጭ ለመላክ ሲሞከር የመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ አቶ ጌታሁን የጉምሩክ ባለሥልጣን ከኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በ1996/97 በተፈራረመው የመግባቢያ ስምምነት መሰረት እንደዚህ አይነት እቃዎች በፖስታ አገልግሎት ድርጅትና በኤርፖርት በኩል በሕጋዊ መንገድ የሚላኩ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በየብስ መጓጓዣ ወደ ውጭ መላክ ስለመቻሉ የተገለፀ ነገር አለመኖሩን አብራርተዋል፡፡ በዚህም መሠረት እቃው በቁጥጥር ሥር ውሎ ለሚመለከተው አካል ማለትም ለኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ለመላክ ዝግጅት መደረጉን አቶ ጌታሁን አስታውቀዋል፡፡ ይህንኑ በተመለከተ ለጉምሩክ ባለሥልጣን የኦፕሬሽን መምሪያ ክፍል ማሳወቃቸውን ገልፀዋል፡፡ የእቃው ባለቤት የባንክ ፐርሚት (መፍቀጃ) ቢኖረውም፤ በስምምነቱ መሠረት እንዲህ ያለ እቃ ወደ ውጭ ስለመላኩ በግልጽ ባለመገለፁ በቁጥጥር ሥር ውሎ የማጣራት እርምጃ እንዲካሄድ መደረጉን አቶ ጌታሁን አስታውቀዋል፡፡ እቃው እንዲያልፍ ፈቃድ መስጠት ያለበት ባለሥልጣኑ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ጌታሁን፤ "እኛ ጋር እንደዚህ አይነት እቃ በየብስ ወደ ውጭ እንዲላክ የሚፈቅድ መመሪያ የለም" ብለዋል፡፡ ጋላፊ በኢትዮጵያና በጅቡቲ ድንበር ላይ የሚገኝ በመሆኑ፣ ኤክስፖርት የሚደረግ እቃ ፍተሻ የሚደረገው ጋላፊ ላይ መሆኑንና እስከዛሬ በተደረገ ፍተሻ ንዋየ ቅዱሳንና የባህላዊ የቅርስ እቃዎች ተይዞ እንደማያውቅ አብራርተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ውሳኔውን የኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን እንዲወስን እቃው በወታደር ታጅቦ ወደ አዲስ አበባ እንደሚላክ አቶ ጌታሁን አስታውቀዋል፡፡ በተሾመ ንቁ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |