| የውጪ አገር ባለሃብቶች በ60... |
|
|
| Wednesday, 23 April 2008 | |
|
የውጪ አገር ባለሃብቶች በ60 ቢሊዮን ብር ካፒታል የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወሰዱ
በማምረቻ ኢንዱስትሪ የተሰማሩት ይበዛሉ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 59.5 ቢሊዮን ብር ካፒታል ላላቸው 1ሺ 240 ፕሮጀክቶች ላቀፉ የውጭ አገር ባለሃብቶች ፈቃድ ሰጠ፡፡ ባለሀብቶቹ በብዛት የተሰማሩት በማምረቻ ኢንዱስትሪዎች መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በኤጀንሲው የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽንና ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር አቶ አክሊሉ ወ/ማርያም ለሪፖርተር ጋዜጣ እንደገለፁት ከሐምሌ 1 ቀን 1999 እስከ መጋቢት 30 ቀን 2000 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት የኢንቨስትመንት ፈቃድ የወሰዱት 1ሺህ 240 ፕሮጀክቶች ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ402 ፕሮጀክቶች እና በ19.3 ቢሊዮን ብር ካፒታል ዕድገት አሳይተዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ ሙሉ በሙሉ ሥራ ለ544ሺ 934 ኢትዮጵያውያን የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩ የገለፁት አቶ አክሊሉ ክልላዊ ሥርጭታቸው ሲታይ ከግማሽ የማያንሱት በአዲስ አበባ ሆነው የተቀሩት በቅደም ተከተል በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በአማራ፣ በድሬዳዋ፣ በትግራይ የተሰማሩ ናቸው፡፡ ፕሮጀክቶቹ የዘርፍ ሥርጭታቸው ሲታይ ማምረቻ ኢንዱስትሪ በ24.6 ቢሊዮን ብር 381 ፕሮጀክቶችን በመያዝ መሪ ሆኗል፡፡ በቀጣይ በ12.4 ቢሊዮን ብር 245 ፕሮጀክቶች በሕንፃ ግንባታ (ሪል ስቴትን ጨምሮ)፣ ሲሆን በ11.3 ቢሊዮን ብር 245 የግብርና ፕሮጀክቶች በሶስተኛ ደረጃ የውጪ ባለሃብቶቹን ትኩረት ስቧል፡፡ በአራተኛ ደረጃ ሆቴልና ቱሪዝም በ9.2 ቢሊዮን ብር ካፒታል 124 ፕሮጀክቶች ፈቃድ ወስደዋል፡፡ የውጪ ባለሃብቶች ትኩረት በተለይ በማምረቻ ኢንዱስትሪዎች መሆኑ ከመንግሥት ፍላጎት ጋር የተጣጣመ መሆኑን አቶ አክሊሉ ጠቁመው የባለሃብቶቹ ቁጥር በየዓመቱ ዕድገትና መሻሻል ማሳየቱ ለኢንቨስትመንት ምቹ ፖሊሲ መኖሩን ያሳያል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ መዋዕለንዋያቸውን ያፈሰሱ ባለሀብቶች በቅደም ተከተል ከአውሮፓ፣ ከእስያ፣ ከአሜሪካና ከመሳሰሉ አገራት የመጡ መሆናቸውን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል፡፡ በጋዜጣው ሪፖርተር |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |