| ክቡር ሚኒስትር |
|
|
| Wednesday, 23 April 2008 | |
|
ክቡር ሚኒስትር እንዲያው አቤት የምንልበት ቦታ አጥተን ነው፡፡ እርስዎ ጉዳዩን ይረዳሉ ንገርዋቸው ተብለን ነው የደወልነው፡፡
- ምንድነው ችግሩ? - ክቡር ሚኒስትር ይኸውልዎት ልናለማው የወሰድነውን መሬት ሊነጥቁን ነው፡፡ - ማን ነው የሚነጥቃችሁ? - ክልሉ ነዋ! - መቼ ነበር መሬቱን የወሰዳችሁት? - ከስድስት ዓመት በፊት ነበር፣ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - እንዴት እስካሁን ድረስ ሳይወስድ ቀረ ታዲያ? - እንዴት ክቡር ሚኒስትር? - እናለማለን ብላችሁ መሬት ስትወስዱኮ ገበሬ ተፈናቅሎ ነው፤ ለእናንተ መሬቱ የተሰጠው፡፡ ወይ እናንተ አልሰራችሁበት ወይ ገበሬው አልተጠቀመበት፡፡ ለመሆኑ ስንት ካሬ ሜትር ነው? - አንድ ሚሊዮን ካሬ ሜትር ነው፡፡ ከአርሶ አደሮች አይደለም የወሰድነው ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ከማን ነው ታዲያ? - ጣሊያኖች ሊያለሙት ነበር፡፡ የዓለም ባንክ ብዙ ገንዘብ አፍሶበታል፡፡ ልናለማው ከእነሱ ተነጥቆ ለእኛ ተሰጥቶ ነበር፡፡ - ይህ ከሆነማ ብቻ ሳይሆን መታሰርም አለባችሁ፡፡ - ክቡር ሚኒስትር መሬቱ የማን እንደሆነ አውቀዋል? - ይኸው ነገርከኝኮ፡፡ - አይደለም፡፡ እኔኮ የእሳቸው ሰራተኛ ነኝ እንጂ የመሬቱ ባለቤት አይደለሁም፡፡ ባለቤቱ ማን እንደሆነ ያውቃሉ? - አላውቅም፡፡ - ክቡር ሚኒስትር፣ የሰውየው ነው፡፡ - ማን ነው ሰውየው? - እንዴ ክቡር ሚኒስትር እያወቁት" - አላውቅም፣ አላውቅም፣ አወቅኩም አላወቅኩም ለውጥ የለውም፡፡ መሬቱን ለማልማት አልቻላችሁም፡፡ በቃ፡፡ - ክቡር ሚኒስትር ሰውየውኮ በየቦታው ብዙ ልማት ይሰራሉ፡፡ ስለበዛባቸው ነው፡፡ - ታዲያ የምትውጡትን ያህል አኝኳ" የማታለሙትን አትውሰዱ፡፡ ገና ለገና ታለማላችሁ እየተባለ ሕዝብ መጎዳት የለበትም፡፡ - ክቡር ሚኒስትር፣ ሕዝቡ እንዳይጎዳማ የፊታችን እሑድ ለሕዝቡ ትልቅ ድግስ አዘጋጅተናል፡፡ - ምን የሚሉት ድግስ? - አስር ሺህ ለሚሆን የአካባቢው ሕዝብ በሬ ታርዶ እንጀራ ቀርቦ በነፃ እንዲበላ፡፡ - ስማ! - አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡ ስለልማት እያወራን ስለምፅዋት ለምን ታወራለህ? - ክቡር ሚኒስትር ሰውየው ለሕዝቡ ያላቸው ፍቅር መግለጫ ነው፡፡ - በል እንግዲያውስ እኔ ስለልማት እንጂ ስለፍቅር ስለማላውቅ ሌላ ሰው ጋ ደውል፡፡ - ክቡር ሚኒስትር".እ". (ስልኩ ተዘጋ፡፡ ከሰዓታት በኋላ እንደገና ተደወለላቸው) - አቤት፡፡ - ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ጤና ይስጥልኝ ማን ልበል? - በአካል አያውቁኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡ ጧት አንድ ሰው ደውሎዎልዎት ነበር፡፡ አልተግባባችሁም መሰለኝ፡፡ ሰውየው ሃሳቡን መግለፅ አይችልም፡፡ ይቅርታ" ጉዳዩን ለማሳወቅ ነው የደወልኩት፡፡ ሰውየው ራሳቸው እኔ እንድደውል ስላዘዙኝ ነው፡፡ - ማን ናቸው ሰውየው? - እርስዎ ያውቃሉ ብለን ስለምናምን ነው ዝርዝር ውስጥ የማንገባው፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - እስቲ ወደ ጉዳይህ ግባ ምንድነው የፈለግከው? - ለልማት የወሰድነውን መሬት ክልሉ ሊነጥቀን - ለልማት ኖሮ ባለማኸው ነበርኮ፡፡ - ቦታኮ ብዙ ልማት እያካሄድን ነው፡፡ በሌላ ቦታ ያለውም ይሄኔ ታጥሮ ቀርቶ ይሆናል፡፡ - አልገባኝም፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - እናለማለን ብሎ መሬት ወስዶ አጥሮ መርሳትና አለማልማት በብዛት እየታየ ነው፡፡ ስለዚህ መቀማቱ ትክክል ነው፡፡ - በአገር ልማት መቀለድ አይሆንም? ክቡር ሚኒስትር፡፡ - አዎን በአገር ልማት መቀለድ ነው፡፡ ጥያቄው ቀልደኛው ማን ነው የሚለው ነው፡፡ - ክቡር ሚኒስትር እኔ ዋናው ምክንያት ለነገ ማታ እራት ሰውየው ራሳቸው እንዳይቀሩብኝ ብለው ስለጋበዝዎት አደራ ለማለት ነው፡፡ ውጭ ሆነው አሁን ደውለውልኝ ነው፡፡ ዛሬ ይመጣሉ፤ ግብዣው ለነገ ነው፡፡ - ይቅርታ እኔ ደግሞ ነገ ወደውጭ እሄዳለሁ፡፡ - ውጭ አገር ልትገናኙ ስለምትችሉ የት አገር ነው የሚሄዱት፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - እንደዚህ ብሎ ነገር አለ እንዴ? ይቅርታ ስልክ እየመጣብኝ ነው፡፡ (ስልኩ ተዘጋ፡፡ ስራቸውን ጨርሰው ቤታቸው ገቡ፡፡ በሞባይላቸው ተደወለላቸው) - አቤት፡፡ - ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡ ራስህ ሚኒስትር ሆነህ እንዴት ክቡር ሚኒስትር ትለኛለህ ካላልከኝ በስተቀር እጅ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ምነው በእጅጉ ተለሳለስክ ዛሬ፡፡ - ይኸውልህ አንድ ጉዳይ ሰምቼ ነው የደወልኩልህ፡፡ ከእነሱ አባባል እንደተረዳሁት ነገሩ የገባህ አልመሰለኝም፡፡ - እንዴት አልገባኝም፤ የተከበሩ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - መሬቱኮ ለሰውየው የተሰጠ ነው፡፡ - እና? - እናማ ሰውየው ለአገር ልማት የሚጠቅሙ ስለሆኑ እንቅፋት እንዳንሆንባቸው ለመምከር ነው የደወልኩልህ፡፡ - ለልማት እንቅፋት ስለሆነ ነውኮ መሬቱ የሚነጠቀው፡፡ - ስማ የሌላ ቢሆን ግድ የለኝም፡፡ ግን የሰውየው ስለሆነ እንዳትሳሳት፡፡ ሰውየው ራሳቸው ከውጭ ደውለውልኝ ነው፡፡ እራት ተጋብዘህም እምቢ ብለሃል አሉ፡፡ - የተከበሩ ሚኒስትር የተከበሩ ተላላኪ ሲሆኑ ያሳዝናል፡፡ - አትቀልድ". በኋላ ይቆጭሃል ብዬ ነው፡፡ ጠጠር አስቸገረኝ ስትለኝ አልነበረም? - አዎን፡፡ - እና ዝም ብለህ ሰውየውን አሳክሙኝ አትላቸውም? ከእልህ ጤና አይሻልህም፡፡ - ወይ ጣጣ፡፡ - እንዴት ወይ ጣጣ፤ በጣም የተገረምክ ትመስላለህ፡፡ እጅግ በጣም ተገርሜያለሁ እንጂ፡፡ - የተገረምከው? - ያ ጋዜጣ “ታዋቂ የተከበሩ ግለሰቦች ባሌስትራ ሆነው ተገኙ” ብሎ የፃፈው ምን ያህል ትክክለኛ እንደሆነ ገርሞኝ ነው፡፡ - እሺ ቻው፡፡ - ቻው! ከጥቂት ጊዜ በኋላ ስልክ ተደወለላቸው) - አቤት፡፡ - ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር በማታ ደወልኩ፡፡ ካልተኙ ደውል ተብዬ ነው፡፡ - ምን ልታዘዝ? - ይኸውልዎት ክቡር ሚኒስትር፣ እርስዎን ጉዳዩ በቀጥታ ላይመለከትዎት ይችላል፡፡ በክልል የሚወሰን ነው፡፡ ነገር ግን ሰዎች እየደወሉ የእርስዎን ስም እየጠሩ አትንጠቁ ተብሏል ይላሉ፡፡ - የእኔ እንዴት ተነሳ? - አይነጠቁ ብለዋል እያሉ፡፡ - የት ደውለው? እኔ ጋ ብዙ ሰዎች ደውለውልኝ ነበር፡፡ የማይለማ መሬት መነጠቅ አለበት ነው ያልኩት፡፡ ለሚያለማማ ይሰጥ፡፡ እኔ እናንተ በክልል ደረጃ የወሰናችሁትን ውሳኔ እደግፈዋለሁ፡፡ ይነጠቁ ነው ያልኩት፡፡ አይነጠቁ አላልኩም፡፡ የሌላ ሚኒስትር ስም ጠርተውላችሁ እንዳይሆን፡፡ - ሌሎቹኮ እናውቃቸዋለን፡፡ እርስዎ ንፁህ ሰው ነዎት እየተባለ ከእርስዎ መጣ ሲባል ገርሞኝ ነው፡፡ - እንኳን ይህ ሌላም አጥረው ያስቀመጡት ካለ ቢቀሙ ደስ ይለኛል፡፡ - ክቡር ሚኒስትር በእኛ ክልል ብቻ አምስት ታጥሮ ስምንት ዓመት የቆየም አለ፡፡ - ንጠቋቸው አትቀልዱ በሏቸው፡፡ - አመሰግናለሁ፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ ጠንቀቅ ይበሉ፡፡ - መጠንቀቅን ምን አመጣው? - እጅግ በጣም ብዙ ደጋፊ አላቸው፡፡ - የማንቸስተርዩናይትድ ደጋፊ ቢበዛም እየተመለከተ ያደንቃል እንጂ ራሱ ጎል አያገባም፡፡ - አይ፣ አይ ክቡር ሚኒስትር፡፡ እነዚህ ከማንቸስተር ዩናይትድ ደጋፊዎች ለየት ያሉ ውጭ የወጣ ኳስም ጎል ነው ብለው ማስወሰን የሚችሉ ናቸው፡፡ - ስማ የኔ ወንድም፣ እኔ እንጀራ አጥቼ አይደለም ሹመት የተቀበልኩት፡፡ አገሬን ላገልግል ብዬ ነው፡፡ በዚህ በዚህ አገሬን ምን ትርጉም አለው? - አመሰግናለሁ፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ እንዲህ የሚለን ሰው ነው የናፈቀን፡፡ - ደህና እደር፡፡ - ደህና ይደሩ ክቡር ሚኒስትር፡፡ (ክቡር ሚኒስትሩ ጧት ቢሮ ሁለት ሰዎች እየጠበቁዋቸው ነበር፡፡ ፀሐፊያቸው ስትነግራቸው አስገቢያቸው አሉዋት) - ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ጤና ይስጥልኝ፤ ቀጠሮ ነበረን? - አልነበረንም፡፡ ትላንት ግን በስልክ አነጋግረውኝ ነበር፡፡ - ትላንትማ እንኳን ለቀጠሮ ልንስማማ በሃሳብም ተለያይተን ነበር፤ ስልኩን የዘጋነው፡፡ - ነበር፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ ስለሆነ ነው የመጣነው፡፡ በመጀመሪያ ይህችን የፋሲካ ስጦታ ይቀበሉኝ፡፡ - ምንድነው እሱ? - ይኸው (እየፈቱት) ሰዓት ነው፡፡ ክቡር ሚኒስትር ልዩ ዘመናዊና ውድ ሰዓት ነው፡፡ - እኔ ምን ያደርግልኛል? - መቼስ ሚኒስትር ሥራ ይበዛበታል፣ አስሬ ሰዓት ያያል፡፡ ያስፈልጋል ብለን ነው፡፡ የእኛም አይደለም ሰውየው ራሳቸው ናቸው የላኩት፡፡ - እኔኮ ሰዓት አላስርም፡፡ - እንዴት ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ድሮ ሰዓት አስር ነበር፡፡ ሞባይል ከመጣ ወዲህ ግን ሞባይሌ ለመልዕክት ብቻ ሳይሆን ለሰዓትም እጠቀምበታለሁ፡፡ እና". - እና አልፈልግም፡፡ ወደ ቁም ነገሩ እንግባና ምን ፈልጋችሁ ነው? - እርስዎ ከሌሎች ጋር የቅርብ ግንኙነት አለዎት፡፡ መሬቱን እንዳይነጥቁን ያደርጉልን፡፡ ሰውየው ስንት ነገር ለአገር ሰርተዋል፡፡ - በአጋጣሚ ከክልሉ ያገኘሁት መረጃ፣ ከክልሉ የወሰዱት ቦታ ሁሉ ታጥሮ ቀርቷል፡፡ ስምንት ዓመት ያስቆጠረም አለ፡፡ - ቢቀማኮ ልማቱ ይቀራል እንጂ የእሳቸውን ያህል ማንም አያለማውም፡፡ - ቻይናዎች እየጠየቁ ናቸው፡፡ ሕንዶችም እንደዚሁ ጠይቀዋል፣ ቱርኮችም፡፡ - እነዚህ ብለው ነው? - በስምንት ዓመት የሚያጥሩ ሳይሆኑ በስምንት ቀን ግንባታ ጀምረው በስምንት ወር የሚጨርሱ ናቸው፡፡ - እኛኮ ክልሉን ለማልማት ብለን ነው እንጂ ክቡር ሚኒስትር፣ ሌሎች ክልሎችኮ እየለመኑን ናቸው፡፡ - ምን ብለው? - የፈለጋችሁትን መሬት ውሰዱና አልሙ ብለው፡፡ - እንዲያውም ይህን ካነሳችሁልን ወዲህ በየክልሉ ስለሳቸው ኢንቨስትመንት ስጠይቅ ነበር፡፡ ሁሉም ታጥረው ተቀምጠዋል ነው ያሉኝ፡፡ - ክቡር ሚኒስትር የለማ የለም የታጠረ ብቻ ነው አሉ? - ያልታጠረም አለ አሉኝ፡፡ - እና በእርስዎ በኩል የውሳኔ ለውጥ የለም ማለት ነው? ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ክልሉ ነው እንጂ እኔኮ አልወስንም፡፡ በግሌ መሬቱ መነጠቅ አለበት ነው የምለው፡፡ - ይህን ሲሉ ሰውየው አይቆጡም ብለው ነው? - ማ ሚኒስትሩ? - አይደለም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሳይሆኑ ራሳቸው፡፡ - ራሳቸው ስትል ማንን ማለትህ ነው? - ሰውየው፡፡ - ወይ ሰውየው.... |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |