| ከ1ዐዐ በላይ የሚሆኑ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ... |
|
| Thursday, 10 January 2008 | |
|
ከ1ዐዐ በላይ የሚሆኑ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋሉ በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በብሔር በመቧደን በተነሳ የተማሪዎች ግጭት የተሳተፉ መቶ በላይ ተማሪዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉን የጋሞ ጐፋ ዞን መምሪያ ለሪፖርተር አስታወቀ፡፡ የጋሞ ጐፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ጌቱ አለሜ በሰጡት መግለጫ የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች በብሔር በሁለት ጐራ በመቧደን ባነሱት ጠብ ምክንያት ትምህርት መቋረጡን ገልፀዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ካለፈው ሰኞ ጀምሮ ለሦስት ቀናት ትምህርት ተቋርጦ እንደነበር ታውቋል፡፡ በሁለት ቡድን የተቧደኑት ተማሪዎች ድንጋይና መሰል ቁሳቁሶችን በመጠቀም ጠብ ማንሳታቸው ተጠቁሟል፡፡ በግጭቱ አራት ተማሪዎች በተወረወረ ድንጋይ መጠነኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ኢንስፔክተር ጌቱ አለሜ አመልክተዋል፡፡ በግርግሩ ወቅት ሲሸሹ ከነበሩ ተማሪዎች ወድቀው የተጐዱ እንዳሉም ኢንስፔክተሩ ገልፀዋል፡፡ ኢንስፔክተር ጌቱ በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት አለመድረሱን ተናግረዋል፡፡ እንደ አዛዡ ገለፃ ግጭቱን ለማብረድ የዞን ፖሊስ፣ የከተማ ፖሊስ፣ የአድማ በታኝ ፖሊሶችና የፌዴራል ፖሊስ አባላት መሳተፋቸውን ገልፀዋል፡፡ ግጭቱ እንዳያገረሽ ከሠላሳ በላይ የፖሊስ ኃይል አባላት በፈረቃ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ጥበቃ እያደረጉ መሆኑን አክለው ገልፀዋል፡፡ ኢንስፔክተር ጌቱ አለሜ በግጭቱ የተሳተፉ ከአንድ መቶ በላይ ተማሪዎች በቁጥጥር ስር ውለው ፖሊስ ጣቢያ ማረፋቸውን ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ የማጣራት ሥራ እየሰራ መሆኑንም አክለው አስታውቀዋል፡፡ በተሾመ ንቁ |
|
| Last Updated ( Friday, 11 January 2008 ) |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |