| የንግድና ዘርፍ ማህበራት የአገልግሎት... |
|
|
| Wednesday, 30 April 2008 | |
|
የንግድና ዘርፍ ማህበራት የአገልግሎት አሰጣጡን ሊለውጥ ነው
በዳዊት ታዬ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ለአባላት የሚሰጠውን አገልግሎት ለማሻሻልና አባላትን የበለጠ ተጠቃሚ ሊሆኑበት ያስችላል ያለውን አዲስ አሰራር ለመተግበር በዝግጅት ላይ መሆኑ አስታወቀ፡፡ የም/ቤቱ ሃላፊዎች ለሪፖርተር ጋዜጣ እንደገለፁት፣ ም/ቤቱ እስከ ዛሬ አሰራሩ በሁሉም አይነት ሥራ ለተሠማሩ አባላቱ የሚሰጠው አገልግሎት ተመሳሳይ እንደነበር አስታውሰው አሁን ሊተገብር ባቀደው አሰራር ግን አባላት በተሰማሩበት የንግድ መስክ በተናጠል አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያደርግ ነው፡፡ በአዲሱ አሰራር መሰረት የም/ቤቱ አባላት በአስራ አንድ የተለያዩ ዘርፎች በመከፋፈል በየዘርፎቻቸው አማካኝነት አገልግሎት እንዲያገኙ ይደረጋል፡ የም/ቤቱ አባላት በተለያየ ንግድ ውስጥ የተሰማሩና ያሉባቸውም ችግሮች የተለያዩ በመሆናቸው በየዘርፋቸው ተከፋፍለው ከም/ቤቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎትና እገዛ እንዲቀላጠፍ ማድረግ ተገቢ በመሆኑ ምክር ቤቱ እዚህ ውሳኔ ላይ ሊደርስ መቻሉ ተገል"ል፡፡ በእቅዱ መሰረት በአስራ አንዱ የተለያዩ ሴክተሮች የተከፋፈሉት አባላት በየዘርፉ የራሳቸውን ኮሚቴ እንዲመርጡና ይህንን አዲስ አሰራር ለመተግበርም ከአስራ አንዱ ሴክተሮች መካከል አንዱ የሆነው የአስመጪዎች ዘርፍ የመጀመሪያውን ስብሰባ ያደርጋል፡፡ ግንቦት 7 ቀን 2000 ዓ.ም በሚካሄደው በዚሁ ስብሰባ አስመጪ የሆኑ የም/ቤቱ አባላት የራሳቸውን ኮሚቴ እንዲያዋቅሩና ሥራ እንዲጀምሩ የሚደረግ ሲሆን በቀጣይነትም ሌሎች ሴክተሮች ይህንኑ አሰራር እንዲከተሉ የሚደረግ መሆኑን እኚሁ ሃላፊዎቹ አስታውቀዋል፡፡ በም/ቤቱ ሃላፊዎች ገለፃ መሰረት ከሆነ ም/ቤቱ ይህንን የአሰራር ለውጥ በማድረግ ሥራ መጀመሩ ኢትዮጵያ የአለም አቀፉ የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን እያደረገች ካለው ዝግጅት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የም/ቤቱ አባላት በየዘርፋቸው የሚያዋቅሩት ኮሚቴ ኢትዮጵያ የአለም አቀፍ የንግድ ድርጅት አባል ብትሆን ዘርፋቸው ሊያጋጥመው የሚችለውን ችግርና ሊያገኘው የሚችለውን ጥቅም እንዲጠና የሚያስችል ሲሆን እያንዳንዱ ሴክተር ውስጥ ሊገጥም የሚችለውን ችግር ለመንግሥት በማቅረብ ጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጥበት ትልቅ ሚና ይኖረዋል የሚል እምነት አላቸው፡፡ በሌላ በኩልም የም/ቤቱ አባላትና የንግድ ህብረተሰቡ ኢትዮጵያ የአለም ንግድ ድርጅት አባል ብትሆን ምን ማድረግ እንዳለባቸውም ይህ አዲስ አሰራር እገዛ እንደሚያደርግ ተጠቁሟል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |