| የዲያስፖራ ፖሊሲ ለማውጣት ጥናት ተጀመረ |
|
|
| Sunday, 04 May 2008 | |
|
በጋዜጣው ሪፖርተር
በውጪ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና በትውልድ ኢትዮጵያዊያንን የኢንቨስትመንት እና የልማት ተሳትፎ ይበልጥ ለማሳደግ በቀጣዩ ዓመት አገራዊ የዲያስፖራ ፖሊሲ ለማውጣት ዝግጅት በመደረግ ላይ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በውጪ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያኖች ገዳዮች ዳይሬክቶሬት ተ/ዳይሬክተር አቶ ደመቀ አጥናፉ እንደተናገሩት አገራዊ የዲያስፖራ ፖሊሲ ለማውጣት ያስፈለገው እስካሁን የወጡና በሥራ ላይ ያሉ ፖሊሲዎችን ይበልጥ ምቹ ለማድረግ፣ የውጪ አገር ጠቃሚ ተሞክሮዎችን ለማካተት ታስቦ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የጥናት ሥራው በመከናወን ላይ እንደሚገኝ ጥናቱም በቀጣዩ በጀት ዓመት ተጠናቆ ረቂቅ ሕጉ ለፓርላማ ይቀርባል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ በ2000 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት በሰባት ቢሊዮን ብር ካፒታል 671 ያህል ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በኢንቨስትመንትና በልማት መሳተፋቸውን፣ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገቡም ከ62ሺ በላይ ሰዎች የሥራ እድል እንደሚፈጥሩም አቶ ደመቀ ገልፀዋል፡፡ በያዝነው የበጀት ዓመት በአራት ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ ከውጪ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በሐዋላ ወደ ኢትዮጵያ የላኩት ገንዘብ 200 ሚሊዮን ዶላር እንደነበር፣ ከዚህ በፊት ብሔራዊ ባንክ የተሻሻለ መመሪያ ከማውጣቱ በፊት በዓመት 400 ሚሊዮን ዶላር ገደማ መላኩን በመግለጽ የአሁኑ የተሻለ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በተያያዘም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ ለመጣው የፀጥታ ሁኔታ ጋር በተያያዘ በቤይሩት እና በሶሪያ በሕጋዊ መንገድ ሠራተኞች የመላክ ሥራ መቆሙን አስታውቀዋል፡፡ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ከሚመለከታቸው መሥሪያ ቤቶች ጋር በመተባበር ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ጉዞውን ሊያቋርጥ የተገደደው ኢትዮጵያውያኑ የሚገጥማቸውን ችግሮች በፀጥታ መናጋት ምክንያት ለመፍታት ባለመቻሉ ነው፡፡ እንደ አቶ ደመቀ አባባል ከሆነ ኢትዮጵያውያን ይህን ሁኔታ በመገንዘብ ከሕገወጥ ጉዞዎች ራሳቸውን እንዲያቅቡ፣ ስለሚሄዱበት አገራት ከውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ወይም ከሠራተኛ ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተገቢውን መረጃ እንዲጠይቁ መክረዋል፡፡ አቶ ኢሳያስ ጎታ በሚኒስቴሩ የኢኮኖሚ ትብብርና ቢዝነስ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ተ/ዳይሬክተር በኢኮኖሚና በቢዝነስ ጉዳዮች ስለተደረጉ እንቅስቃሴዎች ተጨማሪ መረጃ ለጋዜጠኞች ሰጥተዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |