|
Sunday, 04 May 2008 |
|
በኦስትሪያ በሕፃናት ላይ የሚደርስ ፆታዊ ጥቃት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የሚያሳዩ ሪፖርቶች በቢቢሲ ተላለፈዋል፡፡ ከሪፖርቶቹ መካከል ሴት ልጁን ለሃያ አራት ዓመታት ከምድር በታች በሚገኝ መኖሪያ ቤቱ ውስጥ እስረኛ በማድረግ ወሲባዊ ጥቃት ሲፈጽምባት እንደነበር ይገልፃል፡፡ በ24 ዓመታት ውስጥም ከልጁ ሰባት ልጆችን እንዳፈራ ታውቋል፡፡ ይህ ድርጊት የተፈፀመው ኦስትሪያ አምስተትን ግዛት ውስጥ ነው፡፡
በእስር ቤቶች ውስጥ ተወልደው ከእናቶቻቸው ጋር በዚያው የሚያድጉ ሕፃናቶች በከፍተኛ ደረጃ ለአእምሮ ሕመም የተጋለጡ እንደሚሆኑ የኦስትሪያ የስነልቦና ባለሙያዎች ተናግረዋል፡፡ የዚህ ዓይነት ክስተቶች መብዛታቸውንና እያንዳንዱ አገር በዚህ ረገድ ሁኔታዎችን መከታተልና መቆጣጠር እንደሚኖርበት ኦስትሪያ ደር ስታንዳርድ ዴይሊ ዘግቧል፡፡
ብዙዎች ይህ ኦስትሪያ ውስጥ እንዴት ሊፈፀም ይችላል? በማለት ይጠይቃሉ፡፡ በኦስትሪያ ዳይ ፕሬስ ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው ጎረቤቶች ይህ አሰቃቂ ድርጊት የተከሰተበት ቤተሰብ ራሱን ከሌላው በማግለል የሚኖርና ብዙዎቹ የአካባቢው ኗሪዎች አባትየው ሞቷል ብለው ያስቡ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ኗሪዎች ተቀራርበው በሚኖሩበት በዚያ አካባቢ ይህ ሁኔታ እጅግ ያልተለመደ መሆኑን ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡
ጆሴፍ የተባለው የልጀቷ አባት ኤልዛቤትን የ18 ዓመት ታዳጊ ሳለች ጀምሮ በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ እስረኛ እንዳደረጋትና ሰባት ልጆችም እንደወለደችለት ከልጆቹም አንዱ እንደሞተ ፖሊስ ገልጿል፡፡ ይህ በዲ.ኤን.ኤ ምርመራም ተረጋግጧል፡፡
የዚህ ዓይነቱ ድርጊት በአሁኑ ወቅት እንዴት ሊፈፀም ይችላል? የሚለው ጥያቄ በብዙዎች ተፈጥሯል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ በርካቶች እንደሚኖሩም አመላክቷል፡፡
ኤልዛቤት በአሁኑ ወቅት የ42 ዓመት ሴት ስትሆን ከሁለት ልጆቿ ጋር የስነልቦና ህክምና የምታገኝበት ተቋም ገብታለች፡፡ የኦስትሪያ ወንጀል መርማሪ እንደገለፁት "ግለሰቡ ሁለት ቤተሰብ ያስተዳድሩ ነበር፡፡ ከዋና ሚስታቸው ሰባት ልጆች ያላቸው ሲሆን ልጃቸውና ከሷ የወለዷቸው ስድስት ልጆች ደግሞ በሌላ ቤተሰብ ይመራሉ" ብለዋል፡፡ |