| ከአንድ መቶ በላይ የንግድ ባንክ... |
|
|
| Wednesday, 07 May 2008 | |
|
ከአንድ መቶ በላይ የንግድ ባንክ ሠራተኞች ቅሬታቸውን ለቦርዱ አቀረቡ
በተሾመ ንቁ መንግሥት ለኑሮ ውድነት ማስተካከያ በሚል ከፈቀደው የደሞዝ ጭማሪ በታች ጭማሪ አግኝተናል ያሉ ከአንድ መቶ በላይ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሠራተኞች ቅሬታቸውን ለቦርዱ በፅሁፍ አስታወቁ፡፡ ሠራተኞቹ ከሚያዚያ 13 ቀን 2ዐዐዐ ዓ.ም. ጀምሮ በቡድንና በግል ለባንኩ ቦርድ በፃፉት ደብዳቤ የባንኩ የደሞዝ ጭማሪ አሰራር ላይ ያላቸውን ቅሬታ በፅሁፍ ገልፀዋል፡፡ ሰራተኞቹ የኑሮ ውድነት ማካካሻ የደመወዝ ጭማሪው ከ25 እስከ 33 በመቶ እንደነበረ ነገር ግን የባንኩ አመራር ይህንን ተግባራዊ አለማድረጉን ገልፀዋል፡፡ ሠራተኞቹ ቅሬታቸውን በተመለከተ ለባንኩ የሰው ኃይል አስተዳደር በአካል ቀርበው መጠየቃቸውንና "ከደረጃችሁ በታች ተመድባችሁ ስለምትሰሩ ጭማሪው ከሌሎች እኩል አይሰጣችሁም" የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው አብራርተዋል፡፡ ከደረጃ በታች ስለመመደባቸው የሚገልፅ ማስረጃ አለመኖሩን የጠቀሱት ሠራተኞቹ "የደመወዝ ጭማሪው የኑሮ ውድነትን አስመልክቶ እንጂ የሠራተኛ ትጋትን ወይንም የሥራ መደብን መሠረት ያደረገ አይደለም" በማለት ይከራከራሉ፡፡ የባንኩ የደመወዝ ጭማሪ በባንኩ ለረጅም ዓመታት ያገለገሉ ጥቂት ሠራተኞችን ብቻ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን በመጥቀስ የባንኩ የሥራ አመራር ቦርድ አስፈላጊውን ማስተካከያ በአፋጣኝ እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡ የባንኩ የማስታወቂያና ህዝብ ግንኙነት ክፍል ስራ አስኪያጅ አቶ አየለ ቸርነት ሠራተኞቹ ለቦርዱ የቅሬታ መግለጫ ፅሁፍ ስለማቅረባቸው የባንኩ የሰው ኃይል አስተዳደር መምሪያ እንደማያውቅ ገልፀዋል፡፡ አቶ አየለ ባንኩ የደመወዝ ጭማሪ ያደረገው "ቢያንስ አንድ እርከን ጭማሪ" በሚለው መመሪያ መሠረት መሆኑን አብራርተዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |