| ጤፍ ወደ አሜሪካ በህገወጥ መንገድ ሊላክ ሲል ተያዘ |
|
|
| Wednesday, 07 May 2008 | |
|
በተሾመ ንቁ
ከአንድ ሺህ ኩንታል በላይ ጤፍ በህገ ወጥ መንገድ ወደ አሜሪካ ሊጓጓዝ ሲል በጋላፊ ኬላ ላይ መያዙን የሰሜን ምስራቅ ቀጠና ጉምሩክ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታሁን ቱጂ ለሪፖርተር ጋዜጣ ገለፁ፡፡ አቶ ጌታሁን ቱጂ እንዳሉት በተለያየ መልክ የተዘጋጀ ጤፍ ወደ አሜሪካ ሊላክ ሲል በኬላው ፍተሻ ሠራተኞች ተይዟል፡፡ ከተያዘው የጤፍ ክምችት ውስጥ 717 ኩንታል ጥሬ ጤፍ፣ እንዲሁም ሰባት መቶ ኩንታል በላይ የተፈጨ ጤፍ መሆኑን ሥራ አስኪያጁ ገልፀዋል፡፡ በአቶ ጌታሁን ገለፃ መሠረት አሻሮ፣ ሽሮ፣ በሶ፣ ፉርሽካ በማስመሰል ህገ ወጥ የጤፍ ዝውወር ለማካሄድ ተሞክሯል፡፡ ከአራት መቶ ኩንታል በላይ በ10 ኪሎ ግራም የታሸገ የጤፍ ዱቄት በበሶ መልክ ተዘጋጅቶ ሲወጣ መያዙን እንዲሁም በአሻሮ፣ በሽሮ እና በፉርሽካ ስም ዲኪላራሲዎን የተሞላላቸው ከሦስት መቶ ኩንታል በላይ የተፈጨ ጤፍ ሊወጣ መሞከሩንም አቶ ጌታሁን አብራርተዋል፡፡ የተያዘው የጤፍ ክምችት ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚገመት ሥራ አስኪያጁ ጠቁመዋል፡፡ በቀጠናው የጋላፊ ኬላ በተደረገ ፍተሻ ከጤፍ በተጨማሪ አተር፣ በርበሬ፣ ኑግ፣ ጌሾና ምስር በህገ ወጥ መንገድ ለማውጣት ሲሞከር መያዙን ስራ አስኪያጁ ገልፀዋል፡፡ አቶ ጌታሁን የኢትዮጵያ ጉምሩክ ባለሥልጣን በአዋጅ 368/95 አንቀፅ 67 መሠረት በማጭበርበር ወደ ውጭም ሆነ ወደ ሀገር ውስጥ ሲያስገባ የተያዘ ግለሰብ እቃው ተወርሶ ከ15 እስከ 25 ዓመት እስራት ቅጣት የሚቀጣ መሆኑን ጠቅሰው፤ በህገወጥ ድርጊቱ የተሳተፉ ግለሰቦች በህግ እንደሚቀጡ አስታውቀዋል፡፡ በህገወጥ ድርጊቱ የተሳተፉ የጉምሩክ እና የትራንዚት አገልግሎት ሰራተኞች ላይም ክስ መመስረቱን አቶ ጌታሁን ገልፀዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በህገወጥ መንገድ አንድ ሀያ ፊት ኮንቴይነር ሙሉ የአይሱዙ መኪና መለዋወጫ እቃ ወደ ሀገር ውስጥ ሲገባ ከአንድ ወር በፊት መያዙን አቶ ጌታሁን አስታውቀዋል፡፡ የእቃው ባለቤትም በፖሊስ እየተፈለገ መሆኑን ስራ አስኪያጁ ገልፀዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |