| ተመስገን ዘውዴ ካልተዘጉ ሒሳቦች... |
|
|
| Wednesday, 07 May 2008 | |
|
ተመስገን ዘውዴ ካልተዘጉ ሒሳቦች የተገኘው ገንዘብ እንዲጣራ ጠየቁ
በጋዜጣው ሪፖርተር በመንገድ ሥራና በደመወዝ ጭማሪ ምክንያት ላጋጠመ የገንዘብ እጥረት የአንድ ቢሊዮን 16 ሚሊየን ብር የበጀት ማሟያ ሲጠየቅ ካልተዘጉ ሒሳቦች ከ16ዐ ሚሊዮን ብር በላይ መገኘቱ እንዲጣራ አቶ ተመስገን ዘውዴ ጠየቁ፡፡ ቅንጅትን በመወከል ፓርላማ የሚገኙት አቶ ተመስገን ዘውዴ ከሳምንት በፊት የተጨማሪ በጀት ጥያቄ ጋር ተያይዞ ካልተዘጉ 229 የባንክ ሂሳቦች 160.6 ሚሊየን ብር መገኘቱ፣ 84.5 ሚሊየን ከተዘጉ ሌተር ኦፍ ክሬዲት (ኤልሲ) ሂሳቦች ተገኘ ተብሎ ሪፖርት ቀርቧል ካሉ በኋላ ይኼ እንዴት ሊሆን እንደቻለ ግልፅነት ባለው መልኩ ተገቢውን ማብራሪያ አልተሰጠም ብለዋል፡፡ ይኼንኑ ቅሬታቸውን መሠረት በማድረግ በኢዴአፓ መድኀን ለሚመራው የመንግሥት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ቋሚ ኮሚቴ ደብዳቤ መፃፋቸውን ተናግረዋል፡፡ አቶ ተመስገን ለቋሚ ኮሚቴው የፃፉት ደብዳቤ ይዘት ጉዳይ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ "229 የባንክ ሒሳቦች ላይ ከ160 ሚሊየን ብር በላይ ተገኝቷል ተብሏል፡፡ ሒሳቡ እንዴትና መቼ ተከፈተ፣ በማን ተከፈተ፣ ለምን ተከፈተ፣ እስካሁንስ ሳይታወቅ ለምን ቆየ የሚለው ጉዳይ ላይ በቂ መልስ አላገኘሁበትም፡፡ ስለሆነም ቋሚ ኮሚቴው ተገቢውን ማጣራት እንዲያደርግ ጥቆማ ሰጥቻለሁ" ብለዋል፡፡ በፓርላማ የመንግሥት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ መስፍን መንግሥቱ አቶ ተመስገን ቅሬታቸውን ለቋሚ ኮሚቴው ማቅረባቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ሆኖም ቋሚ ኮሚቴው እንዲህ ዓይነት ቅሬታዎችን እንዴት ይቀበላል፣ እንዴት ያስተናግዳል እና የመሳሰሉ ተያያዥ ጥያቄዎችን ለመፍታት የሚያስችል አሠራር ለመዘርጋት ጥረት እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ፓርላማው ለፌደራል መንግሥት በተጠየቀው ተጨማሪ በጀት ጉዳይ ሚያዚያ 14 ቀን 2000 ተወያይቶ ለሚመለከተው ኮሚቴ መምራቱ ይታወሳል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |