| የሥራ ተቋራጮችና የአማካሪዎች አቅም.... |
|
|
| Wednesday, 07 May 2008 | |
|
የሥራ ተቋራጮችና የአማካሪዎች አቅም ማነስ የቤት ልማቱን ጎድቷል
በኃይሌ ሙሉ መንግሥት ለጀመራቸው የቤቶች ልማት ሥራዎች ከግንባታ ማቴሪያል እጥረት ባሻገር የሥራ ተቋራጮች ተሳትፎ እና አቅም እጅግ አነስተኛ መሆኑ በልማቱ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ማሳደሩን በማጤን መንግሥት ችግሩን ለመቅረፍ እየሠራ መሆኑ ተሰማ፡፡ የፌዴራል የሥራና ከተማ ልማት ሚኒስቴር በ2ዐዐዐ በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት የሥራ እንቅስቃሴ ሪፖርት እንደሚያሳየው ከ1999 በጀት ዓመት ጀምሮ በግንባታ እየተሳተፉ ያሉት የሥራ ተቋራጮች ብዛት 945 ብቻ ሲሆኑ ቁጥሩ ከሚፈለገው አንፃር ሲመዘን አነስተኛ ነው፡፡ በ2000 ዓ.ም. የመጀመሪያ ግማሽ በጀት ዓመት 1 ሺ 585 ሥራ ተቋራጮች ቢያስፈልጉም የተገኙት 1 ሺ 94 ያህል ብቻ ናቸው፡፡ በጠቅላላው 2 ሺ 39 ያህል በቤት ልማት ላይ የሚሳተፉ ተቋራጮች ቢኖሩም ከሚፈለገው አንፃር ሲመዘኑ አሁንም እጥረት እንዳለ ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡ ያሉትም ሥራ ተቋራጮች የአቅም ማነስ ችግርም ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሷል፡፡ በአማካሪዎች ዘርፍም ተመሳሳይ የቁጥር ማነስ፣ የአቅምና ብቃት አነስተኛ መሆኑን ሪፖርቱ ጠቁሞ እነዚህን ችግሮች ለመፍታት "የሥራ ተቋራጮች፣ አማካሪዎችና የግንባታ እቃዎች አቅርቦትና አስተዳደር አቅም ግንባታ እቅድ" ተዘጋጅቶ ተግባራዊ በመሆን ላይ ይገኛል ብሏል፡፡ በእቅዱ መሠረት በያንስ አንድ ሺ አዳዲስ የግል ሥራ ተቋራጮችን ለመፍጠርና ያሉትንም ለማጠናከር ይረዳል፡፡ ያሉትን አማካሪዎች ከማጠናከር ጎን ለጎን 1ዐዐ ያህል አዲስ አማካሪ ድርጅቶችን ለመፍጠርና ለማጠናከር ታስቧል፡፡ በዚሁ እቅድ መሠረት ሥራ ተቋራጮች ያለባቸውን የማሽነሪዎች እጥረት ለመቅረፍ የብድር ሥርዓት መቀረፉን፣ የትራንስፖርት አቅማቸውን ለማሳደግም አንድ ሺ ገልባጭ መኪኖች ተገዝተው በልማቱ እየተሳተፉ ላሉ በብድር መልክ ለማከፋፈል የሚያስችል አሠራር መዘርጋቱን ሪፖርቱ ይጠቅሳል፡፡ በመላ አገሪቱ በ36 ከተሞች እስከ 1999 ዓ.ም. 61 ሺ 427 ቤቶች በመገንባት ላይ መሆናቸው የጠቀሰው ይኸው ሪፖርት ግንባታዎቹ በተለይም በማቴሪያል እጥረት መጓተት እንዳጋጠማቸው ይፋ አድርጓል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |