| ምልዐተ - ጉባኤ ባለመሙላቱ የፓርላማው... |
|
|
| Wednesday, 07 May 2008 | |
ምልዐተ - ጉባኤ ባለመሙላቱ የፓርላማው መደበኛ ስብሰባ ሳይካሄድ ቀረበጋዜጣው ሪፖርተር የኢፌዲሪ ፓርላማ 3ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 28ኛ መደበኛ ስብሰባ ምልዐተ - ጉባኤ (ኮረም) ባለመሙላቱ ምክንያት ትላንት ሳይካሄድ ቀረ፡፡ ፓርላማው ሚያዝያ 28 ቀን 2000 ዓ.ም በሦስት አጀንዳዎች ማለትም የሥራና ከተማ ልማት ሚኒስቴር የ2000 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ ዕቅድ ሪፖርት ማዳመጥ፣ የበጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የፌዴራል መንግሥት ተጨማሪ በጀት ረቂቅ አዋጅን በተመለከተ ያቀረበውን ሪፖርትና የውሳኔ ኅሳብ መርምሮ አዋጁን ማፅደቅ፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንን ለማቋቋም የወጣውን ረቂቅ አዋጅ መርምሮ ለዝርዝር ዕይታ ለሚመለከተው ኮሚቴ መምራት የሚሉ አጀንዳዎች ነበሩት፡፡ ሆኖም ፓርላማው ትላንትና በጠዋቱ ክፍለ ጊዜው አንድ አባል በድንገት በማረፋቸው ምክንያት አስከሬናቸውን ለመሸኘት ሲባል ስብሰባው ወደ ከሰዓት በኋላ የተላለፈ ቢሆንም ከሰዓት በኋላ ከ547 የም/ቤቱ አባላት ግማሽ ያህሉ መገኘት ባለመቻላቸው ሳይካሄድ ቀርቷል፡፡ አፈ ጉባኤ ተሾመ ቶጋ በትላንትናው ዕለት ከሰዓት በኋላ ስብሰባውን ለመጀመር ምልዐተ - ጉባዔ አለመሟላቱን ካረጋገጡ በኋላ የተገኙትን የም/ቤት አባላት ይቅርታ በመጠየቅ ለዛሬ አስቸኳይ ስብሰባ እንደሚጠሩ ተናግረዋል፡፡ አፈ ጉባዔው አያይዘውም የኢሕአዴግ የም/ቤት አባላት ወደኋላ እንዲቀሩ የማስታወቂያ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ አንድ የም/ቤቱ አባል ስለጉዳዩ በሰጡት አስተያየት አንዳንድ የኢሕአዴግ የም/ቤት አባላት የዩኒቨርሲቲና የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በቀኑ ክፍለ ጊዜ እንደሚማሩ፣ አንዳንዶቹም በተለያዩ የመንግሥት የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ያሉ በመሆናቸው በም/ቤቱ መደበኛ ስብሰባዎች ላይ አዘውትረው አይገኙም ብለዋል፡፡ "ባለፉት ሶስት ዓመታት በስብሰባ የኮረም አለመሙላት አጋጥሞኝ አያውቅም" ሲሉ ተናግረዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |