| የዮርዳኖስ አርኪዮሎጂስቶች የመጀመሪያውን... |
|
|
| Sunday, 15 June 2008 | |
የዮርዳኖስ አርኪዮሎጂስቶች የመጀመሪያውን ቤተክርስቲያን ማግኘታቸውን አስታወቁበጋዜጣው ሪፖርተር ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት እንደተገነባ የሚነገርለትን የመጀመሪያውን ቤተክርስቲያን አግኝተናል ሲሉ የዮርዳኖስ አርኪዮሎጂስቶች አስታወቁ፡፡ "ከ33 እስከ 7ዐ ዓ.ም የነበረ የመጀመሪያው ቤተ ክርስቲያን መሆኑን በምርምራችን አረጋግጠናል፡፡ የምናምንበትንም አንደብቅም" በማለት የሪሃብ አርኪዮሎጂካዊ ጥናት ማዕከል ኃላፊ አብዱል ቃድር አል ሁሳን መናገራቸውን ዘ ጆርዳን ታይምስ ዘግቧል፡፡ የመጀመሪያው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በሰሜናዊው ዮርዳኖስ ከሶሪያ ድንበር አቅራቢያ በምትገኘው ሪሃብ ከ23ዐ ዓ.ም. በፊት ከተገነባው የቅዱስ ጐርጐሪዮስ ቤተክርስቲያን አቅራቢያ ተቀብሮ ነበር፡፡ "ቤተክርስቲያኑ 7ዐዎቹ የኢየሱስ ክርስቶስ አርድእት (ደቀመዛሙርት) ማምለኪያ እንደነበረ ማረጋገጫ አግኝተናል" ሲሉ ሚ/ር ሁሳን ተናግረዋል፡፡ "በእግዚአብሔር የተወደዱ 70ዎቹ ደቀመዛሙርት" በማለት በሞዛይክ የተሣሉትና የተገለጹት እነዚህ ደቀመዛሙርት በእምነታቸው ምክንያት በኢየሩሳሌም ይደርስባቸው ከነበረው እንግልትና ስቃይ ለማምለጥ ሲሉ ወደ ሰሜናዊው ዮርዳኖስ በመሰደድ ቤተክርስቲያኑን እንደቆረቆሩ ሚ/ር ሁሳን ገልፀዋል፡፡ ደቀመዛሙርቱም በቤተክርስቲያኑ ውስጥ በመሆን ሃይማኖታዊ ስርዓታቸውን ያከናውኑ እንደነበር በግኝቱ ተረጋግጧል፡፡ የግሪክ ኦርቶዶክስ ሀገረ ስብከት የጳጳሱ ረዳት፣ ሊቀ ካህናት ኒካትሪየስ ግኝቱን አስመልክቶ "በዓለም ለሚገኙ ክርስቲያኖች በሙሉ ማዕዘን ነው" ብለዋል፡፡ ከ3ኛው እስከ 7ተኛው ምእት ዓመት የነበሩ ከሸክላ የተሰሩ የምግብ መመገቢያና ማብሰያዎች አጥኚዎቹ ያገኙ ሲሆን፣ ይህም የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖችና ተከታዮቻቸው በቦታው እስከ መጨረሻዎቹ የሮማውያን አገዛዝ ጊዜ ይኖሩበት እንደነበር አመላካች ነው ተብሏል፡፡ በተገኘው የመጀመሪያ ቤተ ክርስቲያን ዋሻ ውስጥ ለካህናቱ መገልገያ ብዙ የድንጋይ መቀመጫዎች በክብ ቅርፅ ተደርድረው የሚገኙ ሲሆን፣ የውሃ ምንጭ የሆነ ጥልቀት ያለው ቱቦ በቦታው ተገኝቷል፡፡ ሪሃብ 3ዐ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙባት ሥፍራ ስትሆን ድንግል ማርያምና ኢየሱስ ክርስቶስም በቦታው ያልፉበት እንደነበር ይታመናል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |