| ያልተገባው የግብይት ልምድ |
|
|
| Sunday, 15 June 2008 | |
|
በናታን ዳዊት
የዋጋ ንረቱ አንዲህ ተባብሶ የእያንዳንዱ ዜጋ መወያያና ፈታኝ ሳይሆን በፊትም ቢሆን የተለያዩ ምርቶች ሸማቹ ጋር እስኪደርሱ ድረስ በሚደረግ ቅብብሎሽ ሳቢያ የተለያዩ ምርቶች ከዋጋቸው በላይ ሲሸጡ እንመለከታለን፡፡ በተለይ በቀጥታ ለሸማቹ ሊደርሱና አምራቹም በቀጥታ ሸማቹን ሊያገኝባቸው የሚችሉ ምርቶች ሳይቀሩ በመሃከላቸው ሁለት ሶስት ደላላዎች ገብተው ወይም ሰፊ የቅብብሎሽ ሰንሰለት ተዘርግቶ ገበያውን ሲሰቅሉት ማየቱም የተለመደ ነው፡፡ የዚህ አይነቱ የግብይት ልማድ የቆየ ቢሆንም በአሁኑ ወቅትም እንዲህ አይነቱ ተግባራት እንደ ትክክለኛ አሰራር ተወስደው ሲሰራባቸው ማየት ደግሞ ለኑሮ ውደነት መባባስ አንድ ምክንያት መሆናቸው አልቀረም፡፡ ለእንዲህ አይነት ድርጊቶች ብዙ ምሳሌዎችን ማቅረብ የሚቻል ሲሆን ለአሁን ግን በከተማችን ያለውን የሥጋና የከብት ሽያጭን የሚመለከት የታዘብኩትን ለማካፈል እወዳለሁ፡፡ በአሁኑ ወቅት በከተማችን የአንድ ኪሎ ሥጋ ዋጋ በአማካይ የሚሸጥበት ዋጋ ከ45 ብር በላይ በልጧል፡፡ ይህ ዋጋ በአንዳንድ ሥጋ ቤቶች እስከ 60 ብር መድረሱንም ታዝበናል፡፡ የሥጋ ዋጋ ይህንን ያህል የመሰቀሉ ሚስጢር ብዙም ግልጽ ባይሆንም ለስጋ መወደድ የሚሰጡ ምክንያቶች ብዙ ናቸው፡፡ ከልኳንዳ ቤት ሻጮች የሚሰማው የከብት ዋጋ መወደድ ይጠቀሳል፡፡ ሆኖም በከብት ገበያ ላይ የተለየ የተጋነነ የዋጋ ለውጥ እንደሌለ ደግሞ የሚያሳዩ መረጃዎችም አሉ፡፡ ዋጋ ለመቀጠል የልኳንዳ ቤት ባለቤቶች የሚሰጡት ምክንያት እንዳለ ሆኖ በከብት ግብይት ወቅት የሚታየው የግብይት ስርዓት ደግሞ ፈጽሞ ያልታየና የከብት ዋጋ ጨመረ ከተባለ ለጭማሪው ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ተግባራት በእየለቱ ይፈፀማሉ፡፡ ለዚህም ምሳሌ የሚሆነው በአዲስ አበባችን ትልቅ የከብት ግብይት በሚፈጸምበት የቄራ ገበያ ውስጥ የሚፈፀመው ድርጊት ተጠቃሽ ይሆናል፡፡ በዚህ ቄራ አካባቢ ለመታዘብ የቻልኩት በአብዛኛው አንድ ከብት ሲሸጥ በቀጥታ የከብቱ ባለቤት የሆነው ገበሬ ወይም ነጋዴ ለመሸጥ ያለው እድል አነስተኛ መሆን ነው፡፡ ከብቱ መሸጫው አካባቢ ከደረሰ በኋላ የደላሎቹ እጅ ውስጥ ይገባል፡፡ ዋጋ የመተመኑም ስልጣን በአብዛኛው የደላላ ነው፡፡ ገበሬው ወይም ነጋዴውም ለእዛ አካባቢ ደላሎች የተገዙ ስለሚሆኑ የተባሉትን ይፈጽማሉ፡፡ ለማንኛውም እኔ የገጠመኝን በምሳሌ ላስረዳ ሁለት በሬዎችን ይዞ የመጣ አንድ ገበሬ ከብቶቹን ሊሸጥ መጥቶ እንደ ነጋዴ ከሻጮቹ ጋር ተገናኝቶ ለወደደው ሊሸጥ አለመቻሉን ነው፡፡ በሬዎቹ እንደመጡ ደላሎቹ ምን ያህል አንዲሸጥለት እንደሚፈልግ ይጠይቁታል፡፡ ይህንን ያህል ይላቸዋል፡፡ በዚህ አይሸጥም ብለው ትክክለኛውን ዋጋ እንዲናገር እድል የሚሰጠው ቢሆንም ደላሎቹ ከተመኑት ዋጋ ዝንፍ የማይባልበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ለማንኛውም በመገባባትም ይሁን በግድ ለበሬዎቹ ዋጋ ከወጣ በኋላ ደላሎቹ በሬዎቹን ይረከባሉ፡፡ ገበሬው ወይም እንግዳ ነጋዴው ከብቶቹ እስኪሸጡና የተተመነለት ዋጋ ድረስ ጥግ ይዞ መጠበቅም የተለመደ ነው፡፡ በቄራ" በተለመደው አሰራር አራት ሺህ ብር ለአንድ በሬ እንዲደርሰው የተዋዋለው ገበሬ ወይም ነጋዴ ከዚያ በኋላ ላለው ገበያ ውስጥ አይሳተፍም፡፡ ደላሎቹ በጨበጣ የተረከቡትን በሬ አምስትም ስድስትም ሺህ ብር ሸጠው ለገበሬው የተስማሙትን አራት ሺህ ብር ይሰጣሉ፡፡ እንዲህ ባሉ የግብይት ስርዓት የሚፈፀም በደል የገበያ ስርዓቱን በትክክለኛ መንገድ ለመተግበር አያስችሉም አስፈላጊ ያልሆኑ ጭማሪዎችን እንዲፈጠሩ በማድረግ መጨረሻ ላይ እዳውን እንዲሸከም የሚደረገው ሸማቹ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ በሌላ በኩልም አንዳንድ ልኳንዳ ቤቶች አንድ ሁለት ከብቶችን በቄራ አሳርደው፤ ማሳረዳቸውን የሚያረጋግጥ ወረቀት ከወሰዱ በኋላ በርካሽ ዋጋ ወይም ጤንነታቸው ያልተጠበቀና ያልተመረመሩ ከብቶችን በርካሽ በማስመጣት ከጓሮዋቸው ወይም በሌላ ቦታ አሳርደው በቄራ የታረደ አስመስለው ሲሸጡም ይስተዋላል፡፡ ይህ ድርጊት ከጤና አኳያም ሆነ ከህገወጥነት አንፃር ትልቅ ችግር ቢሆንም ይህንን ችግር ለማቃለል በከብት ገበያዎች አካባቢ ያለው የገበያ ሥርዓት ቢስተካከልና አላስፈላጊ ደላሎች እየገቡ የከብት ቅብብሎሽ ሰንሰለቱ እንዲረዝም በመደረጉ ብቻ በአነስተኛ ዋጋ መሸመት ይችል የነበረው ምርት ዋጋው እንዲሰቀል እያደረገ ነው፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |