| የኮንዶሚኒየም ባለዕድሎች ቤታቸውን... |
|
|
| Wednesday, 02 July 2008 | |
|
የኮንዶሚኒየም ባለዕድሎች ቤታቸውን ሳይረከቡ አንድ ዓመት አለፋቸው
በታምሩ ጽጌ ከአንድ ዓመት በፊት የኮንዶሚኒየም ቤት ዕጣ ደርሷቸው ሙሉ፣ ግማሽና 20 ከመቶ ክፍያ የፈፀሙ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እስካሁን ድረስ ቤታቸውን ባለመረከባቸው በችግር ላይ መሆናቸውን በተለይ ለሪፖርተር ጋዜጣ ገለፁ፡፡ ነዋሪዎቹ በየካ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 11/12 በተለምዶ ባልደራስ (ሲግናል) በመባል በሚታወቀው ቦታ ላይና በመካኒሳ አካባቢ ተገንብተው የተጠናቀቁት የጋራ መኖሪያ ቤቶች ባለዕድሎች ሲሆኑ፣ በ1998 ዓ.ምና በ1999 ዓ.ም ዕጣ ወጥቶላቸው፣ ክፍያ የፈፀሙ ቢሆንም እስካሁን ባለመረከባቸው በችግር ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡ ነዋሪዎቹ ዕጣው እንደደረሳቸው ሙሉ፣ ግማሽና 20 በመቶ ክፍያ በፈፀሙበት ወቅት፣ በቅርቡ ትገባላችሁ (ይሰጣችኋል) መባላቸውን፣ ተከራይተውበት የነበረውን የግለሰብ ቤት እንደሚለቁ በማሳወቃቸው "ቤታችንን ልቀቁልን እኛ ባጣ ቆይ አይደለንም" በሚል ከአከራዮች ጋር በችግር ውስጥ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሰሞኑን ነዋሪዎቹ ተሰባስበው ኮሚቴ በማቋቋም ለቤቶች ልማት ኤጀንሲ ጽሕፈት ቤት ማቅረባቸውን የገለፁ ሲሆን፣ ጽህፈት ቤቱ የሚሰጣቸውን ምላሽ በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽህፈት ቤቱ ሥራውን ሙሉ በሙሉ ከቤቶች ኤጀንሲ ከመረከቡ በፊት በተደጋጋሚ ማመልከቻ ማስገባታቸውን፣ በቅርቡ ለተሰናበተው ጊዜያዊ ባላደራ አስተዳደሩም ማስታወቃቸውን፣ ነገር ግን ምንም ምላሽ ሳያገኙ እስካሁን መቆየቱንና አሁንም በባሰ ችግር ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ "ከእኛ በኋላ ዕጣ የወጣላቸው የሌሎች ክፍለ ከተሞች ባለዕድሎች በሙሉ ተረክበው ግማሾቹ እያከራዩ ግማሾቹም እየኖሩበት ይገኛሉ" ያሉት ነዋሪዎቹ "ለምን የእኛ እንደዘገየና እንደማይሰጠን ግራ ገብቶናል" በማለት ጠይቀዋል፡፡ የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑትን ወ/ሪት ፀዳለ ማሞን አግኝተን ባለዕድሎቹ ለምን ዕጣ ወጥቶላቸው መረከብ እንዳልቻሉ ማብራሪያ እንዲሰጡን ያደረግነው ሙከራ፣ ስብሰባ ላይ ናቸው፣ የሉም፣ መልዕክት ካለ እናደርሳለን በሚል በፀሐፊያቸው በኩል ምላሽ ከማግኘት ውጭ ልናገኛቸው አልቻልንም፡፡ አንዳንድ ምንጮች እንደገለፁት፣ "በየካ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 11/12 የተገነቡት የጋራ መኖሪያ ቤቶች መብራትና ውሃ እንዳልገባላቸው፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድ ሥራ እንዳልተጠናቀቀ፣ ከዋናው አስፋልት ጋር የሚያገናኘው መንገድ ታርሶና ፈራርሶ ሳይጠናቀቅ በመቆሙ ምክንያት ሊያስረክቧቸው እንዳልቻሉ ገልፀዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |