| ለጋዜጠኞች የሥዕል ሒስ... |
|
| Sunday, 20 January 2008 | |
|
ለጋዜጠኞች የሥዕል ሒስ ሥልጠና ሊሰጥ ነው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተዳከመ የመጣውን የሥዕልና ቅርፃ ቅርፅ ትንተናና ሂስ ለማጠናከር ይረዳ ዘንድ ለጋዜጠኞች የሥዕል ሒስ ሥልጠና ለመስጠት መዘጋጀቱን ኢንላይትመንት አርት አካዳሚ አስታወቀ፡፡ የአርት አካዳሚው ዳይሬክተር ሠዓሊ እሸቱ ጥሩነህ የሥዕል ትምህርት ቤቱን ተማሪዎች የሥዕል ሥራ ለማስተዋወቅ ተከፍቶ በነበረው የሥዕል ማሣያ መድረክ እንደተናገሩት፣ በሀገራችን የሥዕልና ቅርፃ ቅርፅ ሙያ የበለጠ እንዲጐለብትና እንዲጠናከር በዘርፉ ያሉትን ባለሙያዎች መተቸትና መሔስ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡ በሠዓሊዎች የሚታዩትን ድክመቶችንና ጥንካሬዎችን ለመናገርና ለመጠቆም ደግሞ ጋዜጠኞች አይነተኛ ሙያ እንዳላቸው የጠቆሙት ዳይሬክተሩ የበለጠ የሥዕል ዕውቀትና መሠረታዊ የሥዕል ሂስ እንዲኖራቸው ለማገዝም ሥልጠና ለመስጠት እንዳቀዱና በቅርቡ ከተለያየ መገናኛ ብዙሃን የተውጣጡ ጋዜጠኞችን እንደሚመለምሉ አስታውቀዋል፡፡ ከሥዕል ሂስ ሥልጠናው በተጨማሪ የአርት ቴራፒ ሥልጠና ለመስጠትም ዕቅድ እንዳላቸው አመልክተዋል፡፡ ባለፈው ሐሙስ በተካሄደው የአርት አካዳሚው የተማሪዎች የሥዕል ማሳያ መድረክ ላይ ከ25 በላይ የሚሆኑ ከሕፃናት እስከ አዋቂ የዕድሜ ክልል የሚገኙ ተማሪዎች ሥራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በተማሪዎቹ ከጊዜ ወደጊዜ የሚታየው መሻሻል ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ ለወላጆቻቸውና ለማህበረሰቡ በማሳየት አስተያየት ለመቀበል ባለመው መድረክ ላይ ተሳታፊ የሆነችው ተማሪ ዮዲት ለሪፖርተር ጋዜጣ እንደገለፀችው መድረኩ መዘጋጀቱ ቤተሰቦቻቸውም ሆኑ ሌላው ህብረተሰብ ያላቸውን መሻሻልና ድክመት እንዲነግራቸው ያስቻለና ለወደፊት ሥራቸው ምን ያህል ዕውቀት እንደገበዩ ለማወቅ ረድቷቸዋል፡፡ በደመቀ ከበደ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Forums |
| Contact Us |