| በጂጂጋ ከተማ በደረሰ ፍንዳታ... |
|
| Wednesday, 01 October 2008 | |
|
በጂጂጋ ከተማ በደረሰ ፍንዳታ አራት ሰዎች ሞቱ፣ ሰባት ቆሰሉ
በታምሩ ጽጌ በሱማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በጂጂጋ ከተማ ውስጥ ከትናንት በስቲያ ከሰዓት በፊት በደረሰ የፍንዳታ አደጋ አራት ሰዎች ሞተው ሰባት ሰዎች ከባድ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው በስፍራው የተገኙ የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ጋዜጣ ገለፁ፡፡ እሑድ መስከረም 18 ቀን 2001 ዓ.ም ከጠዋቱ 4፡30 ሰዓት ሲሆን በከተማው ቀበሌ 03 በተለምዶ አጠራር አፍሪካ ሆቴል አካባቢ በሚገኘው አንድነት ሆቴል በራፍ አካባቢ ፍንዳታው መድረሱን የዓይን እማኞቹ ገልፀዋል፡፡ አደጋ የደረሰው በሆቴሉ በራፍ ፊት ለፊት በሚገኝ አንድ ዛፍ ስር በጀሪካን ውስጥ ተደርጐ የተቀመጠ ፈንጅ መሆኑን የገለፁት እማኞቹ፣ ምናልባት በሰዓት የተሞላ ሳይሆን እንደማይቀር ጥርጥሬያቸውን ተናግረዋል፡፡ ፍንዳታው በደረሰበት ሰዓት በአካባቢው የተገኙ አንድ የባጃጅ ሹፌርና በአንድነት ሆቴል ውስጥ ይስተናገዱ የነበሩ ሦስት ሰዎች ህይወታቸው ማለፉን እማኞቹ ተናግረዋል፡፡ በደረሰው ፍንዳታ የአንድነት ሆቴል በሮችና መስኮቶች መስታዎቶቻቸው መሰባበሩን፣ በአካባቢው ያሉ ቤቶችና ሱቆችም መስታዎቶቻቸው መሰነጣጠቃቸውንና ፈንጂው የተቀመጠበት አስፓልት ወደ ውስጥ ተሰርጉዶ መመልከታቸውን እማኞቹ ገልፀዋል፡፡ ከፍተኛና መጠነኛ ጉዳት የደረሰባቸው ሰባት ሰዎች በሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን፣ ነገር ግን በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ሙሉ መረጃ እንደሌላቸው እማኞቹ ተናግረዋል፡፡ በጂጂጋ ከተማ ከትናንት በስቲያ በደረሰው ፍንዳታ የተጠረጠሩ ሁለት ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን፣ የፈንጂውን ዓይነት ለማወቅ ባለሙያዎች ምርመራ እያደረጉ መሆናቸውን የተናገሩት የዓይን እማኞቹ በንፁሀን ዜጐች ላይ የደረሰው የሞትና የአካል ጉዳት እንዳሳዘናቸው ገልፀው፣ ህብረተሰቡ የሚጠራጠራቸውን ሰዎች ለፖሊስ ጥቆማ በማድረግ ህገወጥ ሥራዎችን በጋራ መከላከል እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Forums |
| Contact Us |