| ስማችንን እናድስ |
|
| Sunday, 06 January 2008 | |
|
በሪፖርተር ጋዜጣ ታህሳስ 20 ቀን 2000 እትም ..የፖለቲካ ፓርቲዎችም ሕዝቡም ካለፈው ምርጫ ይማሩ.. የሚለው ርዕሰ አንቀጽ የሚለው በቅርቡ በሚደረገው የቀበሌና የወረዳ የማሟያ ምርጫ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ሕዝቡ የሚጠበቅባቸውን ግዴታ ሥርዓት ባለውና ሰላምና ፀጥታ በሰፈነበት መልኩ መወጣት እንዳለባቸው ያስገነዝባል፡፡
ሕዝቡ ያገለግሉኛል ብሎ ያመነባቸውን ሰዎች የመምረጥ መብቱ መከበር አለበት፡፡ የምርጫ አስፈፃሚዎችም ምርጫው አርተፊሻል እንዳይሆን ሃላፊነት አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት፣ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽንና የሌሎችም ዓለም አቀፍ ተቋማት መናኸሪያ ስለሆነች የዓለምን ትኩረት ትስባለች፡፡ ከዚህ አኳያ ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎቿ ሁሉ ለቀሩት የአፍሪካ አገሮች በአርአያነት ወይም በሞዴልነት የሚታዩ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ለምርጫው ሲባል በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የሚካሄደው ውይይት እንደምርጫ 97ቱ በስም ማጥፋትና በጥላቻ ላይ የተመሰረተ ሳይሆን በመግባባትና በመከባበር ላይ ያተኮረ መሆን አለበት፡፡ ማንኛውም ተከራካሪ ሃሳቡን በነፃ የማንሸራሸር መብት እንዳለው ሁሉ የሌላውንም ወገን መብት ያለመድፈር ግዴታ እንዳለበት ሊያውቀው ይገባል፡፡ በውይይቱ ወቅት የሚነሱት አከራካሪ ነጥቦችም ገንቢና አስተማሪ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ በተለይ በኢሕአዴግ በኩል ጥንቃቄ ማድረግ ከሚገባው በርካታ ጉዳዮች መካከል አንደኛው በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት በኃላፊነት ያስቀመጣቸው ትናንሽ ንጉሦች የሙስና እንቅስቃሴያቸውን ማስቆም አለበት፡፡ ባለጉዳዩን ከማጉላላት እንዲቆጠቡ ሊያስጠነቅቃቸው እንዲሁም የተቀመጡበት ወንበር ሕዝብን ለማገልገል እንጂ በሕዝብ ለመገልገል አለመሆኑን ሊያስረዳቸው ወይም ሊነግራቸው ይገባል፡፡ ይህንን በሽታ ወደፊት በሚካሄደው ምርጫ ላይ ተፅዕኖ እንዳይፈጥር ማጥራት ይኖርብናል፡፡ ስልጣን የአባት ርስት አይደለም፡፡ ሁሉም ወገኖች ለዴሞክራሲ ቅድሚያ ሰጥተው አሰራራቸውን ማስተካከል ይኖርባቸዋል፡፡ በ1997 የጎደፈውን የአገሪቱ ስም የሚታደስበት አጋጣሚ መሆን አለበት፡፡ መልካሙ አበበ፣ ከፒያሳ |
| < Prev |
|---|
| Home |
| Sections |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Forums |
| Contact Us |