| ለኮንስትራክሽን እቃዎች ግዥ... |
|
|
| Sunday, 27 January 2008 | |
|
ለኮንስትራክሽን እቃዎች ግዥ የ70 በመቶ ብድር ተመቻቸ መንግሥት ለኮንስትራክሽን መሣሪዎችን ለሚያቀርቡ ድርጅቶች የ70 በመቶ ብድር በመፍቀድ መንግስት ለሚያሰራቸው የቤቶች ግንባታ የተለያዩ መሣሪያዎችን እንዲያቀርቡ ሊያደርግ ነው፡፡ ብድሩን ለማግኘት ለአምስት አመት ለፕሮጀክት አገልግሎት መስጠትና ሌሎች አስራ ሁለት መስፈርቶችን ማሟላትን ይጠይቃል፡ የሥራና ከተማ ልማት ሚኒስቴር ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ፣ መንግሥት የቤቶችን ልማት ፕሮግራምን በተያዘለት የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ እንዲረዳው 100 ሎደሮች፣ 100 ክሬሸሮች እና 1000 ገልባጭ ተሽከርካሪዎች ለመግዛትና ለፕሮጀክቱ ለማቅረብ ለሚፈልጉ የ70 በመቶ ብድር እንዳመቻቸ ያመለክታል፡፡ በብድር ግዥው በትላልቅ የድንጋይ መፍጫ ክሬሽሮች ለቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጠጠር የሚያቀርቡና ወደፊትም በዚህ ሥራ ለመሰማራት ፍላጎት ያላቸው ተቋማትና በመንገድ ሥራ የተሰማሩ ተቋራጮችን በዋናነት ተሳታፊ እንዲሆኑ የሚጋብዝ ነው፡፡ መሣሪያዎቹን ገዝተው ለማቅረብ ፈቃደኛ የሆኑ ድርጅቶች ከምዝገባ በኋላም የተሻለ መወዳደሪያ ያቀረቡ ኩባንያዎች ተሽከርካሪዎቹን በብድር እንዲያስገቡ የሚደረግ ሲሆን ዋና መወዳደሪያ ሆኖ የሚቀርበውም ተጠቃሚው ለመግዛት ያቀረበው ሎደርና ክሬሸር ብዛት እና በዝግ ባንክ ሒሳብ ያስቀመጠው መጠን ነው፡፡ የመጨረሻ ውጤትንም በተመለከተ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ የሚታወቅ ሲሆን አሸናፊ የሚሆኑት ኩባንያዎች የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የመጨረሻውን ማጣራት አድርጎ ውሳኔውን ለተጠቃሚዎች የሚያሳውቅ መሆኑንም ለመረዳት ተችሏል፡፡ ማሟላት ያለባቸውን መስፈርቶችም በዝርዝር አስቀምጧል፡፡ በዚህ የብድር ግዥ ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈልጉ 12 የተለያዩ መስፈርቶችን ማሟላት እንደሚኖርባቸው ያመለከተው መግለጫው በመስፈርትነት ከተጠቀሱት ውስጥ ድርጅቶቹ ከባንኮች የወሰዱትን ብድር በውለታቸው መሠረት ሳይዛነፍ በትክክል የከፈሉ ወይም በወቅቱ እየከፈሉ የሚገኙ እና ለዚህም ማስረጃ ማቅረብ የሚችሉ መሆን እንዳለባቸውና መሳሪያዎቹን ለማስመጣት የተስማሙ ኩባንያዎችም አካውንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቻ መክፈት እንዳለባቸው ያመለክታል፡፡ ከዚህም ሌላ የወሰዱትን ብድር በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ በየወሩ እኩል በተከፈለ አከፋፈል ሥርዓት ለመክፈል ዝግጁ የሆኑ፣ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ወይም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተለያየ ወቅት የሚያደርገው ማሻሻያ እንደተጠበቀ ሆኖ የወለድ ክፍያ መጠኑ 8.5 በመቶ እንደሚሆን ያሳያል፡፡ ከወለድ አከፋፈሉ ጋር በተያያዘም 8.5 በመቶ ወለድ ለመክፈል የተስማማ የወለድ አከፋፈል አሰራሩን የጣሰ ተበዳሪ ከብድሩ ወለድ መጠን በተጨማሪ በ3 በመቶ ቅጣት እንዲከፍል የሚደረግ በመሆኑ ድርጅቶቹ እነዚህን ሁሉ መስፈርቶች ለማሟላት ዝግጁ መሆን እንደሚጠበቅባቸው መግለጫው ያሳስባል፡፡ በመስፈርቶቹ መሰረት እቃዎቹን ለመግዛት የተስማሙ ኩባንያዎች ከጥር 15 ቀን ጀምሮ በመዝገብ ላይ ሲሆኑ ምዝገባው ጥር 28 ቀን እንደሚያበቃ ታውቋል፡፡ በዳዊት ታዬ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |