Lost Password? No account yet? Register
  • Increase font size
  • Decrease font size
  • Default font size
  • default color
  • red color
  • green color

Reporter - Amharic Version     

Sunday
May 18th
Home arrow Sections arrow ክቡር ሚኒስትር
ክቡር ሚኒስትር Print E-mail
Wednesday, 06 February 2008
 /መንግሥት የሕዝብ ግንኙነት ሥራን ለማጠናከር በሁሉም መስክ አስፈላጊ ኢንፎርሜሽን እንዲሰበሰብና አዲስ የመረጃ ድረ ገፅ እንዲከፈት በወሰነው መሰረት በክቡር ሚኒስትሩ የሚመራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ያሰባሰበውን መረጃ በማጠናቀር ለካቢኔ ሪፖርት እያዘጋጀ ነው/

- በሉ፣ በሉ ሁሉም መረጃ ዌብ ሳይት ላይ ጫኑ፡፡ ጊዜ የለንም፡፡ በአገራችን ያለው የኤች.አይ.ቪ/ኤድስን ሁኔታ በሚመለከት ያለውን ተጨባጭ አሃዝ ጫናችሁ?
- ኧረ d ገና ነን፡፡
- ለምን? ፍጥነት ያስፈልጋል ብዬ አልነበረም፡፡ የዘገያችሁበትን ምክንያት ኋላ በፅሁፍ ታቀርባላችሁ፡፡ አሁን ግን ጫኑት፡፡
- ችግሩ እሱ አይደለም፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ችግሩ እሱ ነው፡፡ ሌላ ችግር የለም፡፡ መረጃ እንደልብ ነው፡፡
- አይደለም፣ አይደለም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምንድን ነው ችግሩ?
- ይኸውልዎት ክቡር ሚኒስትር፣ ከጤና ጥበቃ የመጣው መረጃ ይህን ያህል ሰው በኤች.አይ.ቪ እንደተያዘ ያሳያል፡፡
- ትክክል ነዋ፡፡
- ይቆዩ ክቡር ሚኒስትር፣ እዚህ ጋ ደግሞ ከብሄራዊ ኮሚቴ የመጣው እጥፍ ያደርገዋል፡፡ አሃዙ  መቶ በመቶ ይለያያል፡፡ እዚህ ያለው፣ የውጭ ተቋም ያጠናው አሃዝ ደግሞ ሁለት መቶ ጨምሮ አስቀምጦታል፡፡ ይህ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት ደግሞ 50 በመቶ አሃዙን ይቀንሰዋል፡፡
- እና?
- እናማ ክቡር ሚኒስትር የትኛውን አሃዝ ነው ትክክለኛ ብለን የምንጭነው?
- ሁሉንም ጫኑታ፡፡
- እንዴ መሳቂያ ልንሆን?
- ትመሰገናለህ እንጂ ለምን መሳቂያ ትሆናለህ?
- ክቡር ሚኒስትር፣ እርስ በራሱ የሚጣረስ መረጃ እኮ ነው፡፡ አስር ዓይነት የተለያየ አሃዝ ነው ያለው፡፡
- አገራችን በዴሞክራሲ ታምናለች፡፡ የተለያዩ አመለካከቶች ቢንፀባረቁ ምን ችግር አለበት?
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር ስለአሃዝ ነውኮ የምናወራው፡፡
- አሃዝ ከዴሞክራሲ ጋር አይሄድም ያለህ ማነው?
- ዴሞክራሲ አለ ተብሎ እኮ አንዱ የአድዋ ጦርነት በ1888 ዓ.ም ነበር ሲል ሌላው መብት አለኝ ብሎ በ1456 ዓ.ም ነበር ይላል ማለት አይደለም፡፡
- በል በል አትፈላሰፍብኝ፡፡ ይልቁንስ ጊዜ የለም በአስቸኳይ የኢንቨስትመንት መረጃ በሙሉ ዛሬ ጭናችሁ ጨርሱ፡፡
- እሱም ችግር አለበት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- የእናንተ ነገር አሁንስ አልገባ አለኝ፡፡ ስራ ነው የያዛችሁት ቀልድ ወይስ የመጣላችሁ መረጃ አላስደሰታችሁም?
- እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
- ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት የአስር ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት አገኘች የሚለው አናደዳችሁ እንዴ?
- ክቡር ሚኒስትር፣ እሱም ቢሆን ብር እንጂ ዶላር ሊሆን አይችልም፡፡ በአንድ ዓመት ያን ያህል ዶላር ማለት መቶ ቢሊዮን ብር ማለት ነው፡፡
- ታዲያ ብር አድርጉትና ጫኑታ፡፡
- እሱ ብቻም አይደለም፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እሺ ሌላ ምን አለ ታዲያ?
- ክቡር ሚኒስትር የተገኘ ኢንቨስትመንት ማለትና የተመዘገበ የኢንቨስትመንት ጥያቄ ማለት አንድ አይደለም፡፡
- በል ለያያቸው፡፡
- ለመመዝገብ ሁሉም ሊመዘገብ ይችላል፡፡ ተመዘገበ ማለት ግን ሥራ ላይ ዋለ ማለት አይደለም፡፡
- ለምን ሥራ ላይ አይውልም? ተመዘገበ ማለት ወደ ኢንቨስትመንት ገባ ማለት ነው፡፡
- አይደለም፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡ ገንዘብ አጥሮት የሚተው አለ፡፡ ቢሮክራሲው አሰልችቶት ትቶ የሚወጣ ዲያስፖራና የውጭ ኢንቨስተር አለ፡፡ ኢንቨስተር ለመምሰል ለጉራ ብቻ ወረቀት የሚይዝ አለ፡፡
- አንተ አሉታዊው እንጂ አዎንታዊው አይታይህም፡፡ በል በል ጫነው፡፡
- ኧረ በኋላ መሳቂያ እንሆናለን፡፡
- ሲሳቅብን እናርመዋለን፡፡ እንዲያውም የኢንቨስትመን ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ምን ያህል መሬት ለእርሻና ለኢንቨስተር የተዘጋጀ እንደሆነም ጫኑት፡፡
- መረጃውስ?
- በቀደም በእኔ ፊርማ መረጃ ስጡን ብለን ለክልሎች በሙሉ ልከን የለም ወይ?
- ተልኳል፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እና?
- መልስ ግን አልተገኘም፡፡
- አንድም መልስ የለም?
- ሲዘጋጅ ይላክላችኋል አሉን፡፡
- በደንብ ጫን አድርጋችሁ ስለማትጠይቁ ነዋ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር፣ እንኳን ራቅ ያሉት እዚህ አዲስ አበባ ያሉት ሚኒስትር መስሪያ ቤቶችምኮ መረጃ ላኩልን ብለናቸው አላልኩም፡፡
- ያገኟታላ..
- የእርስዎ ሚኒስትር መስሪያ ቤት ጭምር አላከም፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እኔስ እዚህ ኮሚቴውን ስለምመራ የቢሮዬን ሥራ ለመስራት ጊዜ ስላጣሁ ነው፡፡ ሌላው ሚኒስትር ምን ሆነ?
- ክቡር ሚኒስትር፣ አሁን ማን ይሙት ኮሚቴ የማይመራ ሚኒስትር አለ?
- ምን ለማለት ፈልገህ ነው?
- ኮሚቴን መሰብሰብ አይደለም ምክንያቱ፣ የፍላጎት አለመኖር እንጅ የጊዜ እጥረት አይደለም ለማለት ፈልጌ ነው፡፡
- አትፈላሰፍብኝ፡፡ አሁን ክልልም ይሁን ሚኒስትር የላከ የለም ነው የምትለኝ?
- የእነሱ አለመላክ ብቻ እኮ አይደለም ችግሩ፡፡ መረጃ እንዲያሰባስቡ ያሰማራናቸውም የሚያመጡት መረጃ የሚያስቅ ነው፡፡
- እንዴት?
- ለምሳሌ እዚህ ላሳይዎት፡፡ በኢትዮጵያ ሃያ የሬዲዮ ጣቢያዎች አሉ የሚል መረጃ ይዘው መጡ፡፡
- እንዴት ሆኖ ሃያ ይሆናል?
- የሙዚቃ ፕሮግራም፣ የኤች.አይ.ቪ ፕሮግራም፣ የቻምበር ፕሮግራም ቆጥረው ሬዲዮ ጣቢያ አደረጉት፡፡
- በል፣ በል አሁን ይጫንና ኋላ ይስተካከላል፡፡ ለካቢኔው ሪፖርት የምናደርግበት ቀን እየተቃረበ ስለሆነ ዝም ብለህ ጫን፡፡ ትምህርት ሚኒስቴርስ ላከ?
- የትምህርት ሚኒስቴር የላከው አለ፡፡ እሱም ምስቅልቅል ያለ ነው፡፡
- አንተ ሰውየ ጤነኛ አይደለህም፡፡ ለምንድን ነው የሚመሰቃቀለው?
- ኮሌጅ፣ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የሚለው የተምታታ ነው፡፡ እውቅና እና ቅድመ እውቅና የሚባለውም የተምታታ ነው፡፡ በትምህርት ላይ አስር ዓይነት የተለያዩ ስታቲስቲክሶች አሉ፡፡ እሱን መጫን መንግሥትን ይጎዳል፡፡
- ለምን?
- በ1995 የተመዘገበ መረጃ ብቻ ነው ያለው ክቡር ሚኒስትር፡፡ በመረጃ ላይ ያለው አመለካከት እጅግ ደካማ ነው፡፡
- ሰማንያ ሚሊዮን ሕዝብ ባላት አገርና አራት ሚሊዮን ህዝብ ባላት ከተማ እየተቀመጥን መረጃ አዋቂ የለም ማለት ስድብ ነው፡፡
- እሱም ራሱ አጠያያቂ ነው፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምኑ?
- ይህ የኢትዮጵያ ሕዝብ 80 ሚሊዮን የአዲስ አበባ ሕዝብ 4 ሚሊዮን የሚለው፡፡
- እንዴት? አገር ያወቀውን፡፡
- በመረጃ መደገፍ አለበት፤ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- በቃ በአንተ አመለካከት ኢትዮጵያ 13 የፀሐይ ወራት አሉዋት የሚለው ካልሆነ ሌላው ሁሉ ማስረጃ የለውም፡፡
- 13 የፀሐይ ወራት የሚለውም አጠራጣሪ ነው፡፡ ዝናቡና ብርዱ አስራ ሶስት የፀሐይ ወራት የሚለውን እየሻረው ነው፡፡
- ለመሆኑ በትክክል ስንት ልጆች እንዳሉህ ታውቃለህ?
- በተለምዶ አራት፣ ያልተነገረኝ ግን የእኔ ልጅ የሆነም ሊኖር ይችላል፡፡
- የተመዘገበው ግን አራት ነው ብለህ በእርግጠኝነት ትናገራለህ፡፡
- ለአገር የማይጠቅም ስለሆነ ነው እንጅ በዌብ ሳይቱ በእርግጠኝነት የምጭነው እሱን ብቻ ነው፡፡
- በል በል አሁን ወሬ አታብዛ፡፡ ምን ይሁን አሁን?
- በቃ ይህ የእኛ ኮሚቴ ፈርሶ ስራው በስታትስቲክስ ቢሮ ወይም በሳይንስና ቴክኖሎጂ ወይም በማስታወቂያ ሚኒስቴር ይካሄዱ፡፡
- ለካቢኔ የምናቀርበው ሪፖርት ይህ ይሁን እያልከኝ ነው?
- በሪፖርቱ ማጠቃለያ ይህ ይቅረብ፡፡
- መደምደሚያ ስለሆነ መግቢያውና ይዘቱ ምን ይሁን?
- መረጃ ማግኘት አስቸጋሪ መሆኑ ራሱ በተጨባጭ ማስረጃ መቅረብ ተጀመረ ማለት ነው፡፡
- የተሰጣችሁን ስራ የመስራት አቅም የላችሁም ቢሉንስ?
- በነገራችን ላይ ክቡር ሚኒስትር፣ እሱም ቢሆን ተጨባጭ መረጃ ነው፡፡
- የፈለገው ይሁን የተገኘውን ጫነው፡፡ ከዛ የአዲስ ድረ ገጽ መመረቂያ ብለን በትልቅ ሆቴል የኮክቴል ግብዣ እናድርግ፡፡ በሂደት ይስተካከላል፡፡ ሁሉንም ባለሥልጣን ጠርተን ስናስመርቅ ያኔ ሁሉም ያደንቁታል፡፡
- በኋላ ሲጋለጥ የራሱ አደጋ አለዋ፡፡ እንደ እንትኑ ይሆናል፡፡
- እንደምኑ?
- በኤክስፖርትነት ዛሬ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሸልሞ በነገታው ባሌስትራውን ወርቅ አስመስሎ በመላክ ተጠርጥሮ እንደታሰረው ሰውዬ ዓይነት፡፡
- አንተ ደግሞ በጎ ነገር አይታይህም፡፡  ሁልጊዜ ኔጌቲቭ፡፡
- መጀመሪያ ግን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ስለ አመራረቁ ብናሳውቅና ራሳቸው መጥተው ቢመርቁት፡፡
- እውነትክን ነው እንደዛ እናደርጋለን፡፡ አሳውቄያለሁም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር መቼ አሳወቁ?
-  ከሶስት ቀን በፊት፡፡
- አልነገሩኝም፡፡
- ይህች ናት ጨዋታ፡፡ አንተነህኮ ለኔ ማሳወቅ ያለብህ እንጅ እኔኮ ላንተ ማሳወቅ የለብኝም፡፡ ካንተ ጋር ስውል ሚኒስትርነቴን ረሳኸው?
- አይደለም፣ አይደለም ክቡር ሚኒስትር ስለአቀራረቡ ተወያይተን የተሻለ ሀሳብ እንዲያቀርቡ ብዬ ነው፡፡ ለመመካከር፡፡
- እ.. እንደዛ ከሆነ እሺ፡፡
- እና ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምን አሉ?
- በሶስት ቀን መልሱ ይነገርሃል ተብያለሁ፡፡
- ሶስተኛ ቀኑኮ ዛሬ ነው፡፡
- አንተ እውነትክን ነው፡፡ ልደውል እንዴ?
- አዎን ይደውሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
ረክቡር ሚኒስትሩ ደወሉሪ
- ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ጤና ይስጥልኝ ደህና ነህ? በቀደም ከሶስት ቀን በኋላ መልስ ይነገርሃል ተብዬ ነበር፡፡ መልስ ተሰጥቶ ከሆነ እስቲ እይልኝና ንገረኝ፡፡
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር ወድያውኮ መልስ ተሰጥቷል፡፡
- መቼ?
- እስቲ የትናንትናው ሄራልድና አዲስ ዘመን ጋዜጣ ይመልከቷቸው፡፡
- እሺ አመሰግናለሁ፡፡
ረስልኩ ተዘጋሪ
- አንተ መልስ ተሰጥቷል አሉ፡፡ እስቲ የትናንትናዎቹን ሄራልድና ዘመን ስጠኝ፡፡ ቶሎ በል፡፡
ረአገላብጠው አዩትሪ
- ኧረ ምንም የለም፡፡ ዜናና ሃተታው ላይ የለም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር አለ፡፡
- የት አለ?
- እዚህ የጨረታ ዓምድ ላይ፡፡
- ምን ይላል እስቲ አንብበው፡፡
- ጨረታ ይላል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን የሚል ጨረታ፡፡
- በኢትዮጵያ ላይ መረጃን ያጠናቀረ አዲስ ድረ ገፅ ስለሚከፈት ይላል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እናስ ከዛስ?
- መረጃ ለማሰባሰብና ድረ ገፁን ለመስራት መረጃውና አቅሙ አለን የምትሉ ይላል፡፡
- እሺ ከዛስ ምን ይላል፡፡
- ተጫረቱ..
 
< Prev   Next >