Lost Password? No account yet? Register
  • Increase font size
  • Decrease font size
  • Default font size
  • default color
  • red color
  • green color

Reporter - Amharic Version     

Sunday
May 18th
Home arrow Sections arrow ወጣቶችን በከተማ ጉዳዮች ላይ ለማሳተፍ
ወጣቶችን በከተማ ጉዳዮች ላይ ለማሳተፍ Print E-mail
Wednesday, 13 February 2008
Image
አቶ መሠለ ትኩዬ
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ግሎካል ፎረም በሚባል ዓለም አቀፍ ድርጅት እንዲሁም በተባበሩት መንግሥታት የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም (ዩ.ኤች- ሃቢታት) መካከል በተደረገ ስምምነት በ1998 ዓ.ም በጉለሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ የተቋቋመውን ደብልዩ ኤ ኤፍ (ዊ አር ዘ ፊውቸር) የሕፃናትና የወጣቶች ማዕከል እንቅስቃሴን በሚመለከት በማህበራዊና ሲቪል ጉዳዮች ቢሮ ተወካይ አቶ መሠለ ትኩዬንና የተመድ የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም ኃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ጥጋቡን አነጋግረናቸዋል፡፡
ግሎካል ፎረም በጦርነት ባለፉ አገሮች (ከተሞች) ያሉ ወጣቶችን በሚኖሩበት ከተማ ማህበራዊ፣ ፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ያላቸውን ተሳትፎ በማሳደግ በተለያዩ የውሳኔ ሂደቶች እንዲሳተፉ ማስቻል በሚል ዓላማ ከመረጣቸው ስድስት ከተሞች መካከል አዲስ አበባ አንዷ በመሆኗ ለዚህ ዓላማ ተግባራዊነት ዊ አር ዘ ፊውቸር የሕፃናትና ወጣቶች ማዕከል በጉለሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ በሚገኘው ክበበ ፀሀይ ሕፃናት ማሳደጊያ ውስጥ ሊቋቋም መቻሉን አቶ መሠለ ገልፀውልናል፡፡

ወጣቶች ራሳቸውን የሚችሉበትን መንገድ ለመቀየስ የተለያዩ የሥራ ፈጠራ ክህሎቶችንና የሙያ ስልጠናዎችን የሚያገኙበትን መንገድ ማመቻቸት፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በከተማ ግብርና፣ በስፖርትና በስነጥበብ እንዲሰለጠኑ በማድረግ ረገድ ማዕከሉ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን የግሎካል ፎረምና የተመድ የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም ለማዕከሉ የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርጉ የፕሮጀክቶች ተፈፃሚነትን የሚከታተለው ደግሞ የአዲስ አበባ ማህበራዊና ሲቪል ጉዳዮች ቢሮ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ማዕከሉ ለሀያ ወጣቶች የመጀመሪያ ዙር የኮምፒውተር ስልጠና የሰጠ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ከዓለም የምግብ ድርጅት ጋር በመተባበር ከተለያዩ ክፍለ ከተሞች ለተውጣጡ ሀያ ወጣቶች የከተማ ግብርና ስልጠና እየተሰጠ ነው፡፡ የተወሰኑ ወጣቶችን በስነ ጥበብ ለማሰልጠን ደግሞ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስነጥበብ ትምህርት ቤት ጋር ተስማምቷል”

ስልጠናው የሚሰጠው ከአስራ ስድስት እስከ ሀያ አራት ባለው የእድሜ ክልል ውስጥ ለሚገኙና 10ኛ ክፍል ላጠናቀቁ ወጣቶች ሲሆን ስልጠና ያገኙ ወጣቶች ከእነሱ በታች ላሉ ታዳጊዎችና ሕፃናት ያገኙትን ልምድ የሚያካፍሉበትና በዚህም የተወሰነ ገቢ የሚያገኙበት ሁኔታ መመቻቸቱን ከአቶ መሠለ ገለፃ ለመረዳት ችለናል፡፡ የማዕከሉ ማኔጅመንት የአዲስ አበባ ወጣቶች ማሕበርን ጨምሮ ከሚመለከታቸው አካላት የተውጣጣ መሆኑን ገልፀውልናል፡፡

ማዕከሉ የሚያደርጋቸውን ማናቸውንም እንቅስቃሴዎች በገንዘብና በቁሳቁስ በመደገፍ ላይ ያሉት ግሎካል ፎረምና የተመድ የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም ሲሆኑ በቀጣይነት ወጣቶችና የከተማ ግብርና ላይ የሚሠሩ ድርጅቶች የወጣቶችን አቅም በመገንባት በኩል በሚደረገው እንቅስቃሴ አጋር እንዲሆኑ ለማድረግ በቅርቡ የሚካሄድ አውደ ጥናት እንደሚኖር ጠቁመዋል፡፡ የተለያዩ አጋር ድርጅቶች በማዕከሉ እንቅስቃሴ ተሳታፊ መሆን ማህበሩ ለበርካታ ወጣቶች ስልጠናዎች እንዲሰጥና የራሱን ገቢ ለማግኘት እንደሚያስችለው አመልክተዋል፡፡

ማዕከሉን በየክፍለ ከተማው ለመክፈት የተለያዩ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ መሆኑን የጠቆሙት አቶ መሠለ የፕሮግራሙ ዓላማ ወጣቶች በተለያዩ በጐ ተግባራት በመሰማራት ራሳቸውን ችለው ከማንኛውም ዓይነት ቀውስ እንዲጠበቁና በሚኖሩበት ከተማ ስለሰላም እንዲዘምሩ ማድረግ ነው ብለዋል፡፡

አቶ ቴዎድሮስ በበኩላቸው ማዕከሉ በተወሰነ መልኩ የተመድ የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም 2005 ላይ ከተሞችና ወጣቶች በሚል የጀመረው እንቅስቃሴ አካል እንደሆነና፣ ከግሎካል ፎረምና ከአዲስ አበባ አስተዳደር ጋር በመሆን በወጣቶችና በሕፃናት ላይ እየሠሩ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ ከተሞችን ለኗሪዎቻቸው ምቹ ለማድረግ በሚደረገው እንቅስቃሴ በቀጣይ ኃላፊነት የሚረከቡ ወጣቶች ላይ ትኩረት ማድረግ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል፡፡

ወጣቶች የተለያዩ የሥራ ክህሎቶችን እንዲያዳብሩ በማድረግ በኩል ማዕከሉ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ ከፍተኛ ነው ሊባል ባይችልም ከተመሠረተበት ጊዜ አንፃር እስከ አሁን የተከናወኑት ተግባሮች ተስፋ ፈንጣቂ መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡

“የማዕከሉን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በሚመለከት ግሎካል ፎረምና የተመድ የመኖሪያ አካባቢዎች ፕሮግራም ከአዲስ አበባ መስተዳድር ጋር ስምምነት አድርገዋል፡፡ የማዕከሉን የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተፈፃሚ በማድረግ አስተዳደሩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የተለያዩ ስምምነቶችን ያደርጋል”

 በማለት በእንቅስቃሴው ቀጥተኛ ተሳታፊ የሚሆኑ አጋር ድርጅቶችን ለማበራከት ከአዲስ አበባ ማህበራዊና ሲቪል ጉዳዮች ቢሮ ጋር በመሆን እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ አቶ ቴዎድሮስ ተናግረዋል፡፡

በምሕረት አስቻለው
 
< Prev   Next >