| የሴቶችን ተሳታፊነት በተግባር ማረጋገጥ፣... |
|
|
| Sunday, 24 February 2008 | |
የሴቶችን ተሳታፊነት በተግባር ማረጋገጥ፣ የአፍሪካ ህብረት ሌላ የቤት ሥራአፍሪካውያን ሴቶች፣ እንደሌላው ዓለም ሴቶች ሁሉ፣ ምናልባትም በባሰ ሁኔታ ከወንዶች ወደ ኋላ ቀርተው ይሆናል፡፡ እንደ የሥራ ዕድል፣ ደመወዝ፣ የሥራ ዕድገት፣ ውሳኔ ሰጪነት፣ ትምህርት ባሉ ወሳኝ አካባቢዎች አሁንም እኩል ተጠቃሚ አይደሉም፡፡ ሆኖም በአፍሪካ ህብረት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ካውንስልን የመሠረቱት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በህብረቱ የተፈጠረውን መልካም አጋጣሚ ተጠቅመው እንቅፋቶችን ተጋፍጠው ከሰሩ 21ኛው ክፍለ ዘመን ለአፍሪካ ሴቶች የተሻለ ነገር ይዞ ሊመጣ ይችላል፡፡ አፍሪካ ህብረት ከሚኖሩት አሥር ኮሚሽነሮች ግማሹ ሴቶች እንዲሆኑ የወሰነው በጁላይ 2ዐዐ2 በደርባን ደቡብ አፍሪካ ከአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ አፍሪካ ህብረት መለወጡን በይፋ ባወጀበት ወቅት ነበር፡፡ ይህ ታሪካዊ ውሳኔ የአፍሪካ መሪዎች ሴቶችን በሥልጣን ቦታዎች ለማስቀመጥና ሥልጣናቸውን ለማጋራት ዝግጁ አይደሉም በሚል ሂስ ሲሰነዝሩ የነበሩትን በሙሉ ያሳፈረ ነበር፡፡ ይኸው ውሳኔም አፍሪካ ህብረት እንደ ወላጅ አባቱ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የመሪዎች ስብስብ ብቻ ሳይሆን አፍሪካውያን ወንዶችና ሴቶች በንቃት የሚሳተፉበት “ሰው ሰው የሚሸት” ድርጅት እንደሆነ የሚያሳይ ነው ተብሎም ነበር፡፡ አፍሪካውያን ወንድና ሴቶች በተሻለ ተቀናጅተው ለአህጉሪቱ አዲስ ተስፋ የሚሠሩበትንም ሁኔታ በተሻለ ያመቻቻል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበት ነበር፡፡ ሆኖም የኮሚሽነርነት ቦታው በአመራር ከፍተኛና የዳበረ የሥራ ልምድና ትምህርት የሚጠይቅ በመሆኑ 5ዐ በመቶ የሚለውን ቦታ የሚያሟሉ በቂ ሴቶች ማግኘቱ ከላይ የተጠቀሰው ውሳኔ እንዳይፈፀም የተረጋገጠ እንቅፋት ሊሆን እንደሚችልም ስጋት ነበር፡፡ ሁሉም ሰው ሊረዳው እንደሚችለው በአብዛኞቹ የአፍሪካ ሀገራት ተጨባጭ ሁኔታዎች ሴቶች ሰለባ የሆኑባቸው ባህላዊ ማህበራዊና የትምህርት ልዩነቶች በእኩል ደረጃዎች ላይ እንዳይገኙ አድርገዋቸዋል፡፡ ከፍ ባሉ የውሳኔ ሰጪነት ቦታዎች እንዳይኖሩም እንቅፋት ሆነውባቸው ቆይተዋል፡፡ በሀገራቸው ደረጃ በውሳኔ ሰጪነት ቦታዎች መሳተፍ ያልቻሉ ሴቶች በክፍለ አህጉራዊና አህጉራዊ ቦታዎች ላይ ጐልተው ወጥተው ይገኛሉ ማለት ዘበት ነው፡፡ ስለሆነም የአፍሪካ ህብረትን ኮሚሽነርነት ቦታዎች እንዲይዙ የሚፈለጉት የላቀ ትምህርትና የሥራ ልምድ ያላቸው ሴቶች በበቂ ሁኔታ ላይገኙ ይችላሉ፡፡ በዲያስፖራ ያሉ አፍሪካውያን ሴቶች መመልከት አንድ መፍትሄ ሊሆን እንደሚችል የሚጠቀስ ሲሆን በደርባኑ ስብሰባም የተጠቀሰው አንዱ ነጥብ በዲያስፖራ የሚገኙ አፍሪካውያኑ በአፍሪካ ህብረት አመራር ውስጥ እንዲሳተፉ ጥሪ ማድረግ የሚገባ መሆኑ ነበር፡፡ የ2ዐዐ2ቱ የህብረቱ ምስረታ 50 በመቶ ለሴቶች የሚል ውሳኔ ተግባራዊ መሆን ባለመቻሉ ብቻ ሳይሆን የህብረቱ አመራር የሥርዓተ ፆታ ጉዳይን እንደዋና ጉዳዩ አድርጐ ሊንቀሳቀስ ባለመቻሉ ባለፈው እዚህ አዲስ አበባ የተካሄደው የመሪዎች ጉባዔ ላይም ቅስቀሳ የተደረገበት አጀንዳ ነበር፡፡ የአፍሪካ ሲቪል ማህበረሰብና የሴቶች እንቅስቃሴ የተሰኘው አካል “ሥርዓተ ፆታ አጀንዳዬ ነው” የተሰኘ ዘመቻ በዚሁ የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ አጀንዳ “የኢንዱስትሪ ልማት ለአፍሪካ፣ ከሥርዓተ ፆታ አንፃር” የሚል መሆኑም ጉዳዩን ለማንሳት አመቺ ነበር፡፡ ይኸው ዘመቻ ከግምት ውስጥ ያስገባው ሌላ ነጥብ ደግሞ የአፍሪካ መሪዎችና መንግሥታት የፆታ እኩልነትን ማረጋገጥ የአፍሪካ ልማት ቀዳሚ አጀንዳ መሆኑን አምነው ይህንኑ ለማረጋገጥ ቃል መግባታቸውን ጭምር ነበር፡፡ ዘመቻው ህብረቱና መሪዎቹ ያለውን የፆታ አለመመጣጠን ለማጥበብ ማድረግ አለባቸው ካሏቸው ነጥቦች መካከል የመጀመሪያው በመላው አፍሪካ ፓርላማ እየተሳተፉ ያሉት ጥቂት ሴቶች ቁጥር አድጐ ሁሉም አባል ሀገራት በሚልኳቸው ተወካዮች የሴቶችን ቁጥር ለመጨመር ትኩረት ሰጥተው መሥራት አለባቸው የሚለው ዋነኛው ነው፡፡ ይኸው የእኩል ተሳትፎ መርህ በህብረቱ የኢኮኖሚ ማህበራዊና ባህል ካውንስል እንዲሁም በአፍሪካ የሰብዓዊ ሰዎች መብቶች ኮሚሽንና በአፍሪካ የሰብዓዊ መብቶች ፍርድ ቤት እንዲደገም ሌላው ጥያቄ ነው፡፡ በሰላምና መረጋጋት በኩል በእርቅና ሰላም አፈላላጊነት በሚላኩ ልዑካን ቡድኖች ውስጥ ሴቶችንም ማሳተፍ እንዲሁም ግጭቶችን በመከላከል በኩል ሴቶች የሚጫወቱትን ሚና መደገፍ ሌላው ለአፍሪካ ህብረት የተሰጠ የቤት ሥራ ነበር፡፡ ለዚህ የተሰጠው ምሳሌ “የአፍሪካ ሴቶች ምክክር በዳርፉር ላይ” (በፌሜስ አፍሪካ ሶሊዳሪቲና በአጋሮቹ የሚካሄድ) የተሰኘው ጥረት ሲሆን ይኸው እንቅስቃሴ ድጋፍ ሊደረግለት እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡ በሰብዓዊ መብት በኩል በአህጉር ደረጃ ሰብዓዊ መብትን ለማረጋገጥና ረገጣዎችን ለማስወገድ የሚሠሩ ድርጅቶችና ሲቪል ማህበረሰብ ተቋማት በህብረቱ ሙሉ ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ዘመቻው ለህብረቱ የቤት ሥራዎቹን ለማስታወስ በላከው መልዕክት ገልጿል፡፡ ሌላው ነጥብ በትምህርት ዕድል ለዜጐች ሁሉ የሚመቻችበትን ሁኔታ ሊያረጋግጡ እንደሚገባ መጠቆሙ ነው፡፡ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኘሮግራሞች በትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ማካተት፣ ሴቶችን በእኩል ደረጃ በትምህርት ቤቶች ለማካተት መጣርና በጀት መድቦ መንቀሳቀስ ጊዜ ሊሰጣቸው የማይገቡ የቤት ሥራዎች እንደሆኑ ተጠቅሷል፡፡ ከአፍሪካ አጠቃላይ ህዝብ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዙት ሴቶች እንደመሆናቸው የኢኮኖሚው አንቀሳቃሾችም ናቸው፡፡ በጥቃቅንና አነስተኛ ንግድ የሚሳተፉ ሴቶችን ለማገዝም የአፍሪካ መንግሥታት ውሀ፣ ኤሌክትሪክ እና መንገድ የመሳሰሉ መሠረተ ልማቶችን በመዘርጋት በኩል የሴቶቹን ንግድና ሥራ ፈጠራ በገጠራማ አካባቢዎችም ለማገዝ ለንቀሳቀሱ እንደሚገባ ሌላው የተጠቀሰ ነጥብ ነበር፡፡ የአፍሪካ ህብረት መንግሥትን መመስረት አህጉሪቱን አዋህዶ ህብረቱን ለማምጣት ወሳኝ መሆኑ የታመነበትን ያህል ሴቶች በውይይቱም ሆነ በመንግሥት ምስረታው ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ በሩ ክፍት ሊሆንላቸው ይገባል፡፡ በአጠቃላይም ህብረቱ ወንድና ሴት ልጆቿ በመተባበር የሚመሰርቷት የተባበረች አፍሪካን እውን በማድረግ ረገድም በትኩርት ሊንቀሳቀስ ይገባል ነው መልዕክቱ የአፍሪካ ህብረት ከሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ባካሄደው 11ኛው የመሪዎች ጉባዔ ከ2ዐዐ3 ጀምሮ ተመርጠው የሥራ ጊዜያቸውን ባጠናቀቁ ኮሚሽነሮች ምትክ አዳዲስ ሴት ኮሚሽነሮችን ሾሟል፡፡ እነኚህም የአልጀሪያዋ ራምታንታኔ ላማምራ የሰላምና ደህንነት ኮሚሽነር ሆነው ሲሾሙ ቀደም ሲል ከተመሳሳይ አገር ቦታውን ይዘው የነበሩት ሰይድ ጃኒት የህብረቱን የዳርፉር ሰላም አስከባሪ ዘመቻን ለመምራት የተሾሙትን ተክተዋል፡፡ በህብረቱ ጉባዔ የተሾሙት ሌላዋ የጋምቢያዋ ጁሊያ ዶሊ ሲሆኑ ቀደም ሲል (ከ2003 ጀምሮ) በያዙት የህብረቱ የፖለቲካ ጉዳዮች ኮሚሽነርነት ቦታ እንዲቀጥሉ በድጋሚ ተመርጠዋል፡፡ የጋቦን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ጂን ፒንግ ደግሞ የህብረቱ ኮሚሽን ሊቀመንበር ሆነዋል፡፡ ህብረቱ በሥልጣን ሴቶችን ለማሳተፍ የሚያደርገው ጥረትና ቀደም ሲል 5ዐ በመቶ ሴቶችን በአመራር ለማሳተፍ የሚያደርገውን ጥረት የምናደንቅ፣ ይህንኑም ለመተግበር መንቀሳቀሱን የምናውቅ ቢሆንም ለአፍሪካ ሴቶች በሁሉም ዘርፍ እኩል ተጠቃሚነት ላይ ግን በርካታ የቤት ሥራዎች ያሉበት መሆኑ ግን ግልፅ ነው፡፡ ሴቶችን እኩል ተጠቃሚ ለማድረግ አይደለም፣ ባህልና ልማዳዊ አስተሳሰብ ከሚያደርስባቸው ከባድ ተፅእኖ ለማላቀቅ ህብረቱ በርካታ የቤት ሥራዎች ይቀሩታል፡፡ በዳርፉርና በኬንያ በተፈጠሩ ቀውሶች ሴቶች ግንባር ቀደም ተጠቂዎች ናቸው፡፡ ሶማሌን ጨምሮ ሰላምና መረጋጋት በጠፋባቸው የአህጉሪቱ ክፍሎች ሴቶች ለተገዶ መደፈር ስደትና ተያያዥ ሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ተጋልጠዋል፡፡ ሰላም ባለባቸው አገሮች የአፍሪካ ሴቶች የቤት ውስጥ ጥቃትን ጨምሮ ለሁሉንም ዓይነት ጥቃት የተዳረጉ ናቸው፡፡ አፍሪካ ከግማሽ በላይ የሚሆነውን ህዝብ የሚይዙት ሴቶች በሁሉም ዘርፍ ከወንዶች ወደ ኋላ የቀሩ ናቸው፡፡ ይህንኑ ለማስተካከልም የአፍሪካ መሪዎች ከባድ የቤት ሥራ አለባቸው፡፡ የአፍሪካ ሴቶች የእኩል የሀብት ተጠቃሚነት ጉዳይም ሌላው በአፍሪካ መንግሥታትና በህብረቱ ላይ የተጋረጠ የቤት ሥራ ነው፡፡ የአፍሪካ ሀገራት ሴት ህፃናት እንደጠለፋና ያለዕድሜ ጋብቻ ካሉ ጐጂ ልማዶች ተላቀው የነገይቷ አፍሪካ ግንባታ ላይ በእኩል ለመሳተፍ እንዲችሉ በትምህርት ማገዝም የመሪዎቹና የሀገራቱ ሌላ የቤት ሥራ ነው፡፡ በቤተልሔም ነጋሽ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |