| ለኢንዱስትሪና ለግንባታ ከ3 ሚሊዮን... |
|
|
| Sunday, 24 February 2008 | |
|
ለኢንዱስትሪና ለግንባታ ከ3 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ እንጨት ያስፈልጋል
ኢትዮጵያ ውስጥ እ.ኤ.አ በ2014 ለኢንዱስትሪው ዘርፍና ለግንባታ ሥራዎች አገልግሎት የሚፈለጉ እንጨቶች መጠን ከ3 ሚሊዮን 700 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ ከፍ እንደሚል በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ድርጅት የደን ምርምር ማዕከል የተካሄድ አንድ ጥናት አመላከተ፡፡ ማዕከሉ በደን ምርምር ኒውስ ሌተሩ ላይ ከቀረበው ከዚሁ ጥናት ለመረዳት እንደተቻለው እስከ ተጠቀሰው ዓመት ድረስ ለኢንዱስትሪ ዘርፍ ሥራዎች የሚያስፈልገው የእንጨት መጠን ወደ 640 ሺህ ሜትር ኪዩብ፣ ለግንባታ ተግባራት ደግሞ ወደ 3.1 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ከፍ ይላል፡፡ የእርሻ መስፋፋትና የሕዝብ ቁጥር ማደግ በደን ተክል ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ማሳደሩን፣ በዚህም የተነሳ በሀገሪቱ የሚገኙ አብዛኞቹ ደኖች ተመንጥረው ለእርሻ አገልግሎት እንዲውሉ መደረጉን፣ በደቡብ እና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የተረፉትም ጥቂት ደኖች በመመንጠር ላይ መሆናቸውን አስረድቷል፡፡ በሀገሪቱ በደጋው ክፍል ከ14 ሚሊዮን ሔክታር በላይ የሆነ መሬት በከፍተኛ ደረጃ መታጠቡን ወይም መሸርሸሩን ጥናቱ ጠቁሞ ስድስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የነበረውም ደን በእርሻ መስፋፋት ሳበያ ሙሉ ለሙሉ መውደሙን አስታውቋል፡፡ ህፃናትና እናቶች የማገዶ እንጨት ፍለጋ ብዙ ርቀት መጓዝ ግድ እንደሆነባቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ እብትና ሌሎች ተረፈ ምርቶች የእርሻ ምርትን ለማሳደግ እንዲቻል ለአፈር ማዳበሪያ መዋል ሲገባቸው ለማገዶ አገልግሎት እየዋሉ መሆኑን አስታውቋል፡፡ የማገዶ ፍላጎትን ለማሟላት እንጨት ዋንኛው የኃይል ምንጭ ሲሆን በተለይም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ 85 ከመቶ ያህሉ የኃይል ምንጭ የሚገኘው ከእንጨት መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህም የተነሳ የማገዶ እንጨት ፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣት፣ በድንገት የሚከሰት የእሳት አደጋና ልቅ የሳር ግጦሽ ለደን መመናመን አስተዋፅኦ ማድረጉ ተገልጿል፡፡ ይህ ሁኔታ በገጠሩ ህዝብ የማገዶ ፍላጎትና ከእንጨት የሚሠሩ ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን የማዘጋጀቱን እንቅስቃሴ አደጋ ላይ እንደጣለው ጥናቱ ገልፆ በስፋት የዛፍ ተከላ ማካሄድ ይህንን ችግር እንደሚቀርፍ እና ለአካባቢ ጥበቃም የጎላ አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ አስረድቷል፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |