| የኤርትራ ተቃዋሚዎች ቴሌቪዥን ስርጭቱን ጀመረ |
|
|
| Wednesday, 27 February 2008 | |
|
በዓረብ ሳት የሚተላለፈው የኤርትራ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ደሃይ ኤርትራ ቴሌቪዥን ኘሮግራም ባለፈው ረቡዕ ስርጭቱን ጀመረ፡፡ ኘሮግራሙ በሳምንት አራት ጊዜ የሚተላለፍ ሲሆን በሁለት ቋንቋዎች ይሰራጫል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ስርጭቱን የጀመረው ደሃይ ኤርትራ ቴሌቪዥን ረቡዕና አርብ በትግርኛ እንዲሁም ማክሰኞና ሐሙስ በአረብኛ ቋንቋ ለግማሽ ሰዓት እንደሚተላለፍ ከኘሮግራሙ አስተዋዋቂዎች ገለፃ ለመረዳት ተችሏል፡፡ “ኤርትራውያን ስለአገራቸው ጉዳይ በአገር ውስጥ ሆነው አስተያየት መስጠት ስለማይችሉ በአገራቸው ያጡትን መብት ከአገር ውጭ ሆነው ስለአገራቸው የመሰላቸውን አስተያየት እንዲሰጡ ለማድረግ ነው” ሲሉ የፕሮግራሙ አስተዋዋቂዎች ተናግረዋል፡፡ በማከልም የኘሮግራሙ አስተዋዋቂዎች የጣቢያው ዓላማ አስመልክተው፣ ኘሮግራሙ “ኤርትራውያን በሻዕቢያ እየደረሰባቸው ያለው ጭቆናና ግፍ ለዓለም ማህበረሰብ ያጋልጣል” ብለዋል፡፡ እንደ ኘሮግራም አስተዋዋቂዎቹ አባባል ደሃይ ኤርትራ ቴሌቪዥን፣ በኤርትራ ውስጥ ያለውን ዙርያ ጥምጥም ችግሮች ማጋለጥ ብቻ ሳይሆን ይህ ችግር የሚወገድበትን ሰላምና ዲሞክራሲ የሰፈነበት አገር ለመፍጠር የሚያስችል መፍትሄዎች ከተለያዩ አካላት የሚቀርብበት ነው፡፡ በዚህ የአገሪቱ አፋኝ ስርዓት የተቃውሞ ትግል የሚስተናገድበት መድረክ፣ የኤርትራ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ የአገሪቱ ምሁራንና ሲቪል ማህበረሰቦች የሚሳተፉበት ኘሮግራም እንደሚሆን አስታዋዋቂዎቹ አስረድተዋል፡፡ ኘሮግራሙ የሚሰራጨው ከኢትዮጵያ ሲሆን፣ ዲሽ የሌላቸው ኤርትራውያን እንዲከታተሉት የሚያስችል ሁኔታ መፈጠሩ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የኤርትራ ዲሞክራሲያዊ ኪዳን የተባለው የአገሪቱ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ህብረት በቅርቡ ባካሄደው ስብሰባ የስደት መንግሥት የማቋቋም ዓላማ እንዳለውና በመጪው መጋቢት ወር ላይ አጠቃላይ ጉባዔ እንደሚያካሂድ መዘገባችን ይታወሳል፡፡ በየማነ ናግሽ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |