| የጃክሮስ ሰለባዎች ያቀረቡት የሰበር... |
|
|
| Sunday, 02 March 2008 | |
|
የጃክሮስ ሰለባዎች ያቀረቡት የሰበር አቤቱታ ያስቀርባል ተባለ
የጃክሮስ ሰለባዎችን በሚመለከት እነ ዶ/ር ጥላሁን መኮንን በሾላ አክስዮን ማኅበር ላይ የመሰረቱት ክስ ፌደራል ፍርድ ቤቶች የማየት ስልጣን አላቸው ወይስ የላቸውም የሚለውን ጭብጥ ለመመርመር የሾላ አክስዮን ማኅበር ነገ መልስ ይዞ እንዲቀርብ ሰበር ችሎት ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ ሾላ አክስዮን ማኅበር በጃክሮስ ሰለባዎች ስም መሬት ከአዲሰ አበባ መስተዳድር ወስዷል የሚሉት እነ ዶ/ር ጥላሁን እነሱም የጃክሮስ ሰለባዎች መሆናቸውን በመጥቀስ ሾላ አክስዮን ማኅበር የወሰደውን ቦታ እንዲሰጣቸው ይጠይቃሉ፡፡ “ቦታውን የወሰድከው በጃክሮስ ሰለባዎች ስም ስለሆነ በሊዝ መሸጥ የለብህም” በሚል በፍርድ ቤት የታገደው ሾላ አክስዮን ማህበር በበኩሉ በሪል ስቴት ስም የተቋቋመ መሆኑን ጠቅሶ የጃክሮስ ሰለባዎች ቦታውን የሚጠይቁበት የህግ ስርዓት እንደሌለ የሚገልጽ መከራከሪያ ያቀርባል፡፡ እነ ዶ/ር ጥላሁን የመሰረቱት ክስ ቦታን የሚመለከት በመሆኑ ጉዳዩ ለአዲስ አበባ ከተማ ነክ ፍርድ ቤቶች እንዲቀርብ ሾላ አክስዮን ማኅበር ጥያቄ ቢያቀርብም ከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ክርክሩን ከመረመረ በኋላ ጉዳዩ የመሪ ፕላን አፈጻጸምን የሚመለከት ስላልሆነ ጉዳዩን የማየት ስልጣን ያለው የፌደራል ፍርድ ቤት ነው የሚል ብይን ከማስተላለፉ በተጨማሪ ሾላ አክስዮን ማኅበርም ቦታውን ለእነ ዶ/ር ጥላሁን ሊያስረክብ እንደሚገባ ወስኖ ነበር፡፡ የከፍተኛውን ፍርድ ቤት ውሳኔ ተከትሎ ሾላ አክስዮን ማኅበርም ወደ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብሏል፡፡ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱም ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ ጉዳዩ ቦታን የሚመለከት በመሆኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ጉዳዩን አይቶ ውሳኔ የመስጠት ስልጣን የለውም በማለት የፌደራል ፍርድ ቤቱ የሰጠውን ውሳኔ ሙሉ በሙሉ ውድቅ አድርጎታል፡፡ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን ውሳኔ የተቃወሙት እነ ዶ/ር ጥላሁን በበኩላቸው የተሻሻለው የአዲስ አበባ ቻርተር ለከተማ ነክ ፍርድ ቤቶች የሰጠው ስልጣን የከተማ መሪ ፕላን አፈፃፀም በሚመለከት የይዞታ ባለመብትነት፣ የፈቃድ አሰጣጥን ወይም የቦታ አጠቃቀምን በተመለከተ ለሚነሱ ጉዳዮች እንጂ ማንኛውንም ቦታን የሚመለከት አለመሆኑን በማብራራት ጉዳዩን ወደ ሰበር ችሎት አቅርበውታል፡፡ ጉዳዩ የቀረበለት የሰበር ችሎትም ጥር 29 ቀን 2000 ዓ.ም በዋለው ችሎት የፌደራል ፍርድ ቤቶች ጉዳዩን የማየት ስልጣን አላቸው ወይስ የላቸውም የሚለውን ጭብጥ ለመመርመር አቤቱታውን አስቀርቦታል፡፡ እግድም ሰጥቷል፡፡ የሾላ አክስዮን ማኅበርም ለነገ የካቲት 24 መልሱን ይዞ እንዲቀርብ ታዟል፡፡ በኃይሌ ሙሉሩ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |