| በንግድ ባንክ የደረሰው ፍንዳታ ጉዳት አላደረሰም |
|
|
| Sunday, 02 March 2008 | |
|
በንግድ ባንክ የአባኮራን ቅርንጫፍ ህንፃ ላይ የደረሰው ፍንዳታ ሳቢያ የህንፃውን መስታወቶች ከመሰባበራቸው ውጪ ምንም አይነት ጉዳት አለማድረሱን ፖሊስ ገለፀ፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የመምሪያ ኃላፊ ኮማንደር ኃይሌ አማረ ለሪፖርተር እንደገለፁት በፍንዳታው ምክንያት በህይወት ላይ አደጋ አልደረሰም፡፡ ባንኩ ላይም የደረሰ የንብረት ዝርፊያ የለም፡፡ አርብ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት አካባቢ የደረሰው ፍንዳታ ከባንኩ ውስጥ ይሁን ውጪ ኃላፊው አልገለፁም፡፡ ፍንዳታው እንደተሰማ ባንኩ ውስጥ የነበሩ ደንበኞችና ሰራተኞች ተደናግጠው እንደነበር የገለፀው ወጣት አምሳሉ “ገንዘብ ላወጣ ባንክ ገባሁ፡፡ ከፍተኛ ፍንዳታ ተሰማ ከዚህ ውጪ የማውቀው ሁለት ሰዓት ሙሉ ባንኩ ውስጥ ቆይቼ ተመዝግቤና አድራሻዬን ሰጥቼ መውጣቴን ነው” ብሏል፡፡ የባንኩ በር ላይ ለዓመታት “ወርቅ መሰል ቀለበት” በመስራት እየሸጠ የሚተዳደር አካል ጉዳተኛ ፍንዳታው እንደተሰማ በድንጋጤ ከወደቀበት ያነሱት የሚያውቁት ናቸው፡፡ ከባንኩ ህንፃ ጎን ከሚገኘው ይርጋ ሆቴል ህንፃ ውስጥ የሉሲ ካፌ አስተናጋጅ ቢኒያም ሞገስ በካሬው ውስጥ የነበሩ ተስተናጋጆች እንደነበሩ፣ ፍንዳታው ሲሰማ ከፍተኛ የጩኸት ድምጽና መደናገጥ ተፈጥሮ እንደነበር ይናገራል፡፡ “አስተናጋጆች ብርጭቆ ሰባብረዋል፡፡ ግን ክፈሉ አልተባሉም” ያለው ቢኒያም የሰማው የፍንዳታ ድምጽ ከፍተኛ ኃይል ያለው እንደመሆኑ አደጋ አለማድረሱ አስገርሞታል፡፡ አርብ የመስጊድ ሰዓት ላይ አንዋር መስጊድና አካባቢው የሚጨናነቅበት ሰዓት ካለፈ በኋላ መሆኑ አደጋውን እንደቀነሰውም ጠቁሟል፡፡ በትናንትናው ዕለት ባንኩ መደበኛ አገልግሎቱን የጀመረ ሲሆን ባንኩ ላይ የመስተዋት መሰባበርና የሻተሮች መበጣጠስ ከመድረሱ ውጪ አንዳችም ችግር እንዳልደረሰ የንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ ባሉበት ኃላፊዎች ተናግረዋል፡፡ እንደ ኃላፊዎቹ ገለፃ አደጋው ከደረሰ ከደቂቃዎች በኋላ ባንኩ ውስጥ ላሉ ደንበኞች አገልግሎት እየተሰጠ ነበር፡፡ ፕሬዚዳንቱ ሰራተኞችን በመዘዋወር ካነጋገሩ በኋላ “እንዲህ ያለው ሽብር ማንንም አይጠቅምም” በማለት ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ አደጋው እንደደረሰ በባንኩ ውስጥ ካገኘው መካከል የጠረጠራቸውን ለምርመራ መውሰዱ ታውቋል፡፡ በአሰግድ ተፈ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |