| የዋጋ መቀነስ ያልታየው ምርቱና... |
|
|
| Sunday, 02 March 2008 | |
የዋጋ መቀነስ ያልታየው ምርቱና የሕዝብ ቁጥር ባለመጣጣሙ ነው?የመሬት ምርታማነት ካለው ሕዝብ ጋር እንዲጣጣምና በምርት ፍላጐትና አቅርቦት መካከል ያለውን ልዩነት ለማስተካከል የአመጋገብና የአመራረት ሂደትን መቀየር ወሳኝ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ተባባሪ ተመራማሪ የሆኑት አቶ ደጃሳ ጂሩ ለሪፖርተር ጋዜጣ እንደገለፁት፣ የግብርና ምርት እድገት እያሳየ የዋጋ መቀነስ ያልታየው ምርቱ ከሕዝብ ቁጥር መጨመር ጋር የተጣጣመ ባለመሆኑና የመሬት ምርታማነት በመቀነሱ ነው፡፡ ስለሆነም የአመራረት ሂደትን ማስተካከል ወሳኝ ነው፡፡ በአብዛኛው አካባቢ ለምግብነት የሚመረቱት ጤፍና ስንዴ መሬት ውስጥ ዘልቀው የመግባትና የስርጭት አቅም ስለሌላቸው የመሬቱ ምርታማነት ከጊዜ ወደጊዜ እንዲቀንስ ማድረጉን ለዚህም ስረ ጥልቅ የሆኑ ቋሚ ምግቦችን ማምረት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አሁን ያለው የማዳበሪያ ዋጋ የደሃ ገበሬዎችን አቅም ያላገናዘበና ከሚመረተው ምርት ዋጋ አብዛኛውን ድርሻ የሚወስድ መሆኑን ጠቁመው ማዳበሪያ ከመጠቀም ጐን ለጐን የተለያዩና በቋሚ ምግብነት የሚውሉ ምርቶችን ማምረት የመሬቱን ምርታማነት በማሳደግ በኩል የሚኖራቸው ሚና ጉልህ እንደሆነም አቶ ደቻሳ ተናግረዋል፡፡ በአነስተኛ ዋጋ የተሻለ ምርታማነት ያላቸው ምርቶች እንደ እንሰት፣ የጐመን ዛፍ በምግብ ይዘታቸው የተሻሉ ከመሆናቸውም በላይ አሁን ባለው የምርት እጥረት የተፈጠረውን የዋጋ ንረት የመቀነስ አቅም እንደሚኖራቸውም አቶ ደቻሳ ተናግረዋል፡፡ የምርምር ሥራዎችን ወደ ታች ለማድረስ የግብርናና ምርምር ኢንስቲትዩት ከሚመለከታቸው የተለያዩ አካላት ጋር በጋራ የሚሠራበትን ሁኔታ ገልፀው በመስሪያ ቤቶች መካከል ያለው ጥምረትና በቅንጅት የመስራት ተነሳሽነት ደካማ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የረዥም ጊዜ አገልግሎት ከሚሰጡ ተክሎች ውጤት ለማግኘት ጊዜ መፍጀቱ አርሶ አደሩን በአጭር ጊዜ ምርት እንዳያገኝ ያግደዋል ብለን ለጠይቅናቸው አቶ ደቻሳ ሲመልሱ፣ በአሁኑ ጊዜ በግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ጥምር ጥናት እየተካሄደ መሆኑንና በረዥም ጊዜ የሚደርሱትንና በአጭር ጊዜ የሚደርሱትን ተክሎች በሚኖራቸው መስተጋብራዊ የምርት ግንኙነት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡ “በጥምር ጥናት አቀናጅቶ መጠቀም ወሳኝ ነው፡፡ ሙሉ በሙሉ በእህል ወይም ቋሚ ተክል ላይ ትኩረት ማድረግ ለአደጋ የተጋለጠ ነው” ብለዋል፡፡ አያይዘውም በአሁኑ ሰዓት የመሬቱ የላይኛው ክፍል መጠረግና ለብዙ ጊዜ ተመሳሳይ ምርቶችን ከማምረት አንፃር የመጣውን የምርታማነት አለማደግ ችግር ለመፍታት ጥምር ግብርና አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ አስተባባሪነት ድሬዳዋ ላይ ባጠኑት ጥናት በሐረርና በትግራይ የደረሰው ድርቅ ከማሽላ መሬት የመምጠጥ ባህርይ ጋር ተያይዞ የመጣ በመሆኑ በብዛት በሚመረትበት አካባቢ የተለያዩ ምርቶችን በጥምረት በማምረት ቀስ በቀስ ድርሻውን መቀነስ አስፈላጊ እንደሆነ አቶ ደቻሳ ተናግረዋል፡፡ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ተመርምረውና ተፈትሸው የሚወጡ የግብርና ምርምር ውጤቶችን የማባዛትም ሆነ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የማድረግ አቅም እንደሌለው ጠቁመው ወደ ታች ለማድረስ የማባዛት ሥራው አቅም ባላቸው የገበሬ ማህበር አባላትና በዘርፉ ዘር በማባዛት ሥራ በተሠማሩ አካላት መሠራቱ በተፈለገው ጊዜ ለአርሶ አደሩ ለማድረስ እንቅፋት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም በጋራ የመሥራት መዋቅርና አደረጃጀት መፍጠር አስፈላጊ ነው፡፡ ምርምሮች ሥራ ላይ እንዲውሉ የምርምር ኤክስቴንሽን አስተላላፊ ኮሚቴ ከግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ ከግብርናና ገጠር ልማት፣ መንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ከተውጣጡ የኮሚቴ አባላት ጋር እንደሚሠራም ተጠቁሟል፡፡ ከአመጋገብ ጋር በተያያዘ የሚወጡ የምርምር ሥራዎችን ወደ ሕብረተሰቡ ለማድረስና ተግባራዊ ለማድረግ የአመጋገብ ስርዓትን በመቀየር በኩል የምግብ ሥርዓት ጥናት በትኩረት ሊሠራበት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡ እንደ አቶ ደቻሳ ገለፃ፣ የጐመን ዛፍ ዓመቱን ሙሉ የሚያፈራና ከደረቅ እስከ እርጥብ ሥነ ምህዳር፣ የተለያየ የማምረት አቅም ባለው የአፈር ዓይነት በስፋት ማልማት ሲቻል የፍሬው 40 በመቶ የምግብ ዘይት ሲኖረው ፋጉሎው ለከብት መኖ ወይም ለውኃ ማጣሪያ አገልግሎት ይውላል፡፡ የንጥረ ነገር ይዘቱ ቫይታሚን ሲ ከብርቱካን በ7 እጥፍ፣ ቫይታሚን ዲ ከካሮት በአራት እጥፍ፣ ብረት ከሆርሰራዲሽ 4 እጥፍ፣ ፖታሺየም ከሙዝ ሁለት እጥፍ፣ ፕሮቲን ከወተት በሁለት እጥፍና ካልሲየም ከወተት 4 እጥፍ የሆነ ይዘት እንዳለው ተናግረዋል፡፡ በቤዛዊት ሥዩም |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |