|
Wednesday, 12 March 2008 |
|
ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ ኮንትሮባንድ ተያዘ
የፌዴራል ጉምሩክ ባለስልጣንና የመከላከያ ሰራዊት በአፋር ክልል በገዳማይቱ ከተማ የተከማቸ 40 ሚሊዮን ብር የሚገመት የኮንትሮባንድ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችና ሸቀጣሸቀጦችን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር አዋሉ፡፡ ኮንትሮባንዱ በተያዘበት ዕለት በጦር መሳሪያ የታጀበ ግጭት ተፈጥሮ ነበር፡፡
ከጉምሩክ ባለስልጣን የተገኘ መረጃ እንደሚያመላክተው ከአዲስ አበባ 300 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው የገዳማይቱ ከተማ በኮንትሮባንድ የተያዘው እቃ ስኳር፣ ዘይት፣ ዲቪዲ፣ ቴሌቪዥን፣ ብርድልብስና የሞባይል ቀፎዎች ናቸው፡፡
የኮንትሮባንድ መዘዋወሪያ በመሆን በምትታወቀው የገዳማይቱ ከተማ የተያዘው ኮንትሮባንድ እቃ የሚገባው በበርበራ ወደብ በኩል ነው፡፡ እቃው በበርበራ ወደብ በኩል ከገባ በኋላ በውስጥ ለውስጥ መንገድ በመኪና ተጓጉዞ ገዳማይቱ ከተማ ይጠራቀምና ወደ አዲስ አበባ ይጫናል በማለት የኮንትሮባንዱን እንቅስቃሴ በፍተሻ ሥራ የተሰማሩ ገልፀዋል፡፡
ከበርበራ ወደ ገዳማይቱ ሲመላለስ የነበረው የኮንትሮባንድ እቃ እስኪጠራቀም የተጠበቀው ሆን ተብሎ እንደነበር የጉምሩክ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ነጋዴዎቹ እቃውን መጋዘን ሲያከማቹ በልዩ ጥበቃ ይደረግ እንደነበር የገለፁት እነዚህ ክፍሎች መጋዘኑ ከበባ ተደርጐበት እቃው በቁጥጥር ስር ሲውል ነጋዴዎቹ ተኩስ በመክፈት ለመከላከል ሞክረው እንደነበር ተናግረዋል፡፡
የካቲት 21 ቀን 2000 ዓ.ም የተከማቸው እቃ በቁጥጥር ስር ሲውል ነጋዴዎቹ ተኩስ በመክፈት በህገወጥ የተከማቸውን ንብረት ለማሸሽ ያደረጉት ሙከራ በሰውና በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያደርሰ በመከላከያ ኃይል በቁጥጥር ስር እንደዋለ ታውቋል፡፡
የመከላከያ ሰራዊትና ጉምሩክ በቁጥጥር ስር ያዋሉትን ንብረት ወደ በርታ የጦር ካምፕ አጓጉዘውታል፡፡ በእለቱ ጊዜያዊ የመንገድ ማሳለፊያ ቅፅ እዛው በማዘጋጀት ወደ አዲስ አበባ ጅምላ ንግድ አስመጪ ድርጅት (ጅንአድ) በማጓጓዝ ገቢ መደረጉን ከእቃ ማዘዋወሪያ ጊዜያዊ ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ጊዜያዊ የእቃ ማሳለፊያ ቅጽ ለአንድ ቀን ብቻ የሚሰራ እንደሆነ፣ እቃውን ጅንአድ ሲረከብ ቅጹንም አብሮ መረከብ እንዳለበት ቅጹ ላይ ተጠቅሷል፡፡ እንደ ጉምሩክ ገለፃ ይህ የተደረገው ቀዳዳውን በመጠቀም ኮንትሮባንድ ነጋዴዎችና አመላላሾች አመሳስለው እንዳይጠቀሙ ነው፡፡
በሌላ ዜና ጉምሩክ በኮንትሮባንድነት የሚይዛቸውን ሸቀጦች እየተረከበ የሚሸጠው ጅንአድ የሚረከብበትና የሚሸጥበት ዋጋ እጅግ የተጋነነ ትርፍ የተካተተበት መሆኑን የጅንአድ የሪፖርተር ምንጮች አስታወቁ፡፡ መረጃ ጠቅሰው ምንጮች እንደጠቆሙት ጉምሩክ በኮንትሮባንድ ከሚይዛቸው ቁሳቁሶች መካከል አንድ ሊትር ዘይት በስድስት ብር ሂሳብ ያስረክባል፡፡ ጅንአድ ደግሞ ሊትሩን በሃያ ብር ሂሳብ ይሸጣል፡፡ ከአንድ ሊትር አስራ አራት ብር ያተርፋል፡፡ በተመሳሳይ 1 ኪሎ ስኳር 2 ብር ከ35 ሳንቲም ገዝቶ እስከ 6 ብር ይሸጣል፣ 172 ብር የገዛውን ዲቪዲ ከሦስት መቶ ብር በላይ ይሸጣል፡፡ እንደ ምንጮቹ በምግብ ሸቀጦች ላይ ጅንአድ ያለአግባብ የሚያገኘውን ትርፍ በመቀነስ በኑሮ ለተጐዱ የህብረተሰብ ክፍሎች ወይም ለመከላከያ ሰራዊት ለምግብነት ቢሰጥ የወጪ በጀት ይቀንሳል፡፡ መንግሥትም በህብረተሰቡ ይመሰገናል ብለዋል፡፡ ጉምሩክ በኮንትሮባንድ የያዘውን እቃ ለጅንአድ እንዲያስረክብ የተደረገው ሙስናን ለመከላከል ታስቦ እንደሆነ አይዘነጋም፡፡
በአሰግድ ተፈራ |