| የወጥ አብዮት?! |
|
|
| Wednesday, 12 March 2008 | |
አንድ ብር ከአምሣ ሳንቲም ሲሽጥ የነበረው ጨው በሰዓታት ውስጥ በኪሎ አስር ብር መሆኑ ባለፈው ዓርብ በአዲስ አበባ ድንጋጤና ንዴት ፈጥሮ ነበር፡፡ መንግሥት ፈጣን እርምጃ በመውሰዱ ምክንያት እንደገና በሰዓታት ውስጥ ወደ ነበረበት መመለሱ ደግሞ ሕዝብ ደስ ቢለውም ከዚሁ ጋር ሌላ ስሜትና ጥያቄ ተፈጥሯል፡፡ ችግሩ የገንዘብ ስግብግብነት ወይስ የስልጣን ስግብግብነት? የሚል ጥያቄን እያስከተለ ነው፡፡ የብረት ዋጋ ጨመረ ሲባል በአንድ ጊዜ ኅብረተሰቡን አያናጋም፡፡ በቀጥታ ከብረት ጋር ሕዝቡ በዕለታዊ ኑሮው አይገናኝምና፡፡ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ ሲባልም በትራንስፖርት ዋጋ መጨመር ሁሉም የሚነካ ቢሆንም ደረጃው ውሱንነት አለው፡፡ ወደ ምግብ ብንገባም የጤፍ፣ የፓስታና የሞኮሮኒ ዋጋ ጨመረ ቢባልም ጤፍና ፓስታ ሳይበላ የሚኖር አለና በሕብረተሰቡ ዘንድ መናጋት ጎልቶ አይታይም፡፡ የጨውና የበርበሬ ጉዳይ ግን ምቱና የመልስ ምቱ ወዲያው ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን የተለያየ ባህልና ቋንቋ አላቸው፡፡ ጨውና በርበሬንም በተለያየ መልኩና አቀራረብ ይጠቀማሉ፡፡ ሃብታም ጨውን የዶሮ ወጥ ለመስራት ይጠቀምበት ይሆናል፡፡ ድሃው ግን በእንጀራ ላይ ነስንሶ ልጆቹን አብልቶ ወደ ትምህርት ቤት ይልካል፡፡ ሃብታም በርበሬን ለጥሬ ስጋ ሊጠቀምበት ይችላል፡፡ ድሃው ግን እንዳለ በደረቁ እንደወጥ ተጠቅሞ ቤተሰቡን ያኖርበታል፡፡ ለዚህም ነው የበርበሬ፣ የጨው ዋጋ ናረ ሲባል ጩኸት የበረከተው፡፡ በቀጥታ ከዕለታዊ ኑሮና አመጋገብ ጋር የተያያዘ ስለሆነ ሃብታሙንም ድሃውንም እንዴት ነው ነገሩ እንዲል አድርጎታል፡፡ ስግብግብ ነጋዴዎች በአንዴ አንድ ሺህ ፐርሰንት ለማትረፍ ፈልገው የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ውጤት ነው ወይስ ጨውና በርበሬ የሕብረተሰቡ የወጥ ጉዳይ ስለሆነ ሕዝቡ የሚበላው አጥቶ ሆ ብሎ በመንግሥት ላይ እንዲነሳና መንግሥትን ገልብጦ ሥልጣን ለመያዝ የሚደረግ የስልጣን ጥመኞች እንቅስቃሴ? የገንዘብ ወይስ የስልጣን ስግብግብነት ወይስ የስልጣን ጥመኝነት? በአቋራጭ ሚሊኒየር ለመሆን ወይስ በአቋራጭ ስልጣን ላይ ቁጢጥ ለማለት? ወይስ የገንዘብ ስግብግብነትና የስልጣን ስግብግብነት የጋራ ግንባር? የገንዘብ ስግብግብነት እንዳለ የተረጋገጠ ነው፡፡ ከበስተጀርባውስ የፖለቲካ ስግብግብነት የስልጣን ጥመኝነት ግፊት እያደረገ ነው ወይ ነው ጥያቄው እንጂ በአንድ ሰዓት ውስጥ በስልክም፣ በሌላም በሌላም የተሰራጨው የጨው መልዕክት በአንድ ጊዜ ከመደርደሪያ የተነሳው በነጋዴው ብቻ ሳይሆን ከበስተጀርባ ሌላ እንዳለ አሳማኝ ምልክት ነው፡፡ በሌላ የፖለቲካ ቅስቀሳ፣ ተደራጅቶና አደራጅቶ፣ በተለይም "ተቀናጅቶ" ለመታገል ወኔውም፣ አመለካከቱም አቅሙም ሲጠፋና ሕዝቡ አልገባም ሲል በወጥ በኩል ገብቶ ሕዝቡን ለማነሳሳት መሞከር ያለ ይመስላል፡፡ የወጥ አብዮት ያልነውም ለዚሁ ነው፡፡ ቀዩ አብዮትና ብርቱካናዊው አብዮት አልሳካ ሲሉ በጨውና በርበሬ በኩል የወጥ አብዮት እየተሞከረ ይመስላል፡፡ ሁሉም ልብ ሊለው ይገባል፡፡ በጨውና በበርበሬ ሕዝቡን ማስቆጣትና ማናደድ ሶስት አበይት መልዕክቶችን ያስተላልፋል፡፡ አንደኛው ለሕዝቡ፣ ሁለተኛው ለመንግሥትና ገዥ ፓርቲ፣ ሶስተኛው በጨውና በርበሬ ማለትም በወጥ በኩል ሕዝቡን ማነሳሳት ለሚሞክሩ፡፡ ለሕዝብ የሚያስተላልፈው መልዕክት ሁኔታውን በትኩረት እንዲከታተለው ነው፡፡ ከአንድ ብር ወደ አሥር ብር፣ ከአሥር ብር ተመልሶ ወደ አንድ ብር የሚመለስ ዋጋ ምክንያቱ እጥረት አልነበረም ማለት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሲፈጠር ሸማቹ ጠንካራ አቋምና ለመብቱ መከራከር አለበት፡፡ የሸማቾች ማኅበርን እየፈጠረ መቆጣጠርና መከላከል አለበት፡፡ በዚህና በዚህ ሕዝቡን መሳሪያ አድርጎ ሊያነሳሳ ለሚፈልገውም ቀይ መብራት ማሳየት ያስፈልጋል፡፡ ሕዝብ የስግብግቦች መሣሪያ እንደማይሆን በግልፅ ሊያሳይ ይገባል፡፡ ሕዝብን መናቅ የትም እንደማያደርስ ሕዝብ መልዕክት ሊያስተላልፍ ይገባል፡፡ ለመንግሥት የሚተላለፈው መልዕክትም ግልፅ ነው፡፡ ማንም ስግብግብ እየመጣ በሕዝብ ላይ ሲቀልድ መንግሥት ሊያድነኝ ይችላል ወይስ አይችልም? የሚል ጥያቄ በሕዝብ ዘንድ እየተነሳ ስለሆነ መንግሥትም ገዢው ፓርቲም ማገናዘብ ይኖርባቸዋል፡፡ የጨው ዋጋ ሲጨምር መንግሥት ያስተካክለዋል የሚል እምነት መኖር አለበት፡፡ ሕዝብ የማንም መጫዎቻ እንደማይሆን በተግባር የ"ያሳይና የ"ጠብቅ መንግሥት እንደሆነ ሊያስመሰክር ይገባል፡፡ በመግለጫ ሳይሆን በተግባር! ለገንዘብና ለፖለቲካ ስግብግብነትም የሚያስተላልፈው መልዕክት አለ፡፡ እንዳሰቡት ሕዝብ መንግሥትን መገልበጥ ሳይሆን በስግብግብና በጥመኞች ላይ ቁጣውን ገል"ል፡፡ በወርቅ፣ ብሔራዊ ባንክ፣ በጨው ጉዳይ በሕዝብ ዘንድ ያለው ስሜት ጥብቅ ነው፡፡ ሃይለኛ እርምጃ ይወሰድባቸው የሚል እንደሆነ መገንዘብ ይበጃል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ መንግሥትም፣ ፖለቲከኛም፣ ነጋዴም፣ ቀይ መስመር እንዲያልፍ አይፈልግም፡፡ በዚህ አትምጣብኝ የሚል ሕዝብ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በዘመነ መሳፍንት የእርስ በርስ ውጊያ ነበር፡፡ የሶማሊያ ወራሪ ሲመጣ በግዛቴ ጉዳይ አትምጡብኝ ብሎ አንድ ሆኖ ተዋጋ፡፡ ደርግ አንድነት አንድነት ሲል ጥሩ አለ፡፡ ለአንድነት ብሎ እጨፈጭፋለሁ ሲል ግን በዚህ አትምጣብኝ አለ፡፡ ኢሕአዴግ ስልጣን ሲይዝ የደርግ ወታደሮችን አባሮ ነበር፡፡ የራሱን ታጋዮችም አፈናቅሎ ነበር፡፡ ቅሬታም ፈጥሮ ነበር፡፡ ሻዕቢያ ወረራ ሲያካሂድ ግን በአገር ጉዳይ አትምጡብኝ ብሎ አንድ ሆነ፡፡ ቅንጅት ሕዝብን አግኝቶ ነበር፡፡ የአዲስ አበባን ሙሉ ድምጽ አግኝቶ ነበር፡፡ ቀብር አትሂዱ፣ ሠርግ አትሂዱ፣ እዚያ አትብሉ እዚያ ሻይ አትጠጡ የሚል በማህተም የተደገፈ መመሪያ ሲያወጣ ግን በዚህ አትምጣብኝ፣ በማህበራዊ ኑሮዬ ያንተ "ማንዋል" አያስፈልገኝም ነው ያለው፡፡ ስለሆነም የወጥ አብዮት ሕዝብ በመንግሥት ላይ እንዲነሳ ያደርግልናል ብለው ተስፋ የሚያደርጉ ካሉ በዚህ አትምጡብኝ ብሎ በእነሱ ላይ ሊነሳ እንደሚችል ቢገነዘቡት ይበጃል፡፡ ስልጣን ይገባኛል የሚል ካለ ፕሮግራሙንና መርሃ ግብሩን አስተካክሎ በአደባባይ ታግሎ ይምጣ እንጂ በወጥ ቤት በኩል ሊሽሎከሎክ አይገባም፡፡ |
| < Prev | Next > |
|---|
“ጦርነት የሚፈጠረው ተቃዋሚዎች...
ምክር ቤቱ ሕንፃውን ለመረከብ...
“ዋጋው ባይረጋጋ እንኳን ነጋዴው...
“ዋጋው ባይረጋጋ እንኳን ነጋዴውመረጋጋት ይኖርበታል”
ወጣቱ ዲን
ራስን ለገበያ ማመቻቸት
"ከረጅም ርቀት ውጭ...
በዚምባብዌ ድጋሚ ምርጫ ይካሄድ ይሆን?
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |
Share your thought and ideas with others on our public forum. Just register here and participate on our new and improved forum. Note that all members of the old version forum have to register again to post on the new version forum.