Lost Password? No account yet? Register
  • Increase font size
  • Decrease font size
  • Default font size
  • default color
  • red color
  • green color

Reporter - Amharic Version     

Friday
May 09th
Home arrow Sections arrow ክቡር ሚኒስትር
ክቡር ሚኒስትር Print E-mail
Wednesday, 12 March 2008
- ሃሎ..
- አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- የለም እንዴ ሰውየው?
- አለ እንጂ ... መጥፎ ወሬም እየተወራ ነው፡፡
- ምን መጥፎ ወሬ?
- የሃሰት ብር ታትሞ ሊገባ ሲል ተይዟል፡፡ ሊያስገባ የሞከረው እሱ ነው የሚል ወሬ አለ፡፡ ሁላችንም ተረብሸናል፡፡
- ቻቻቻቻ .... ው... ው...
(ክቡር ሚኒስትሩ ስልኩን ዘጉትና ብቻቸውን ቢሯቸውን ዘግተው ተቀመጡ፡፡ ፀሐፊዋ ገባች)
- ልግባ ይላል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ማን ነው እሱ?
- የእርስዎ ጓደኛ ወንድም ነው፡፡
- ማን ነው የእኔ ጓደኛ? የምታውቂው ጓደኛ አለ?
- ክቡር ሚኒስትር እርስዎ ራስዎ ታመው ጀርመን ሲሄዱ ተባበረኝ ብለው የነገሩኝ ነዋ..
- ታዲያ እሱ ድሮ ነው፡፡
- እና ይግባ ወይስ?
- ግባ በይው ግን የካቢኔ ስብሰባ ስላላቸው ለአንድ ደቂቃ ብቻ በይው፡፡
- እሺ፡፡

(ሰውየው ገባ)
- ደህና ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
- ደህና ነኝ ምን ልርዳህ?
- ወንድሜ የተፈረመ ደብዳቤ ይሰጡሃል ብሎ ነግሮኝ ለዛ ነው የመጣሁት፡፡
- ገና አልተፈረመም፡፡
- ተፈርሞ ተዘጋጅቷልና ሰው ላክ ብለውኝ ነው ብሎ ነበር የላከኝ፡፡
- መቼ ነው እንደዛ ያለህ?
- ትናንት ነበር ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ታዲያ ዛሬኮ ብደውል ብደውል አጣሁት፡፡
- ፖሊስ ጣቢያ ሄዶ ነው፡፡
- ለምን?
- እንጃ በወርቅ ይሁን በታተመ ብር ብቻ ባንዱ ጠርጥረውት ሊጠይቁት ፈልገው ነው መሰለኝ፡፡ ብቻ እሱን ይጠይቁት፡፡ ማታ ያገኙት የለ የእራት ግብዣ አለ እንዳይረሱ፡፡
- ፖሊሶች ይለቁታል ብለህ ነው?
- እሱ ይችልበታል፡፡ ይሰጣቸዋል፣ ይለቁታል፡፡
- ገንዘብ አሳትሟል የሚባለውስ?
- ቢሆንም ግማሽ፣ ግማሽ እንካፈለው ይላቸዋል፡፡ ይለቁታል፡፡ እሱ አክቲቭ ነው፡፡
- ፖሊሶችም ዘንድሮ ጠንከር ያሉ ይመስላሉ፡፡
- አንድ የመጣሁበት ምክንያትም ፖሊሶቹ ሲወስዱት ለእርስዎ እንድነግር ስለነገረኝ ነው፡፡
- እኔ ምን ማድረግ እችላለሁ?
- መርማሪዎቹን አያውቋቸውም?
- አውቃቸዋለሁ ብለህ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር እርስዎ ይሞክሩ፡፡ በነገራችን ላይ ምንጣፍ ከውጭ ገብቷል፡፡ ዛሬ ውሰድላቸው ስላለ ቤት ልውሰደው?
- ቤ... ትት... ቤት አትውሰደው፡፡ የእህቴን ቤት ታውቀው የለ፡፡ እዛ ውሰደው፡፡ ደብዳቤውንም ለካ ፈርሜዋለሁ፡፡ እንካ ይኸውልህ፡፡
- አመሰግናለሁ ቻው፡፡

(ማታ ወደ ተጋበዙት ግብዣ አልሄዱም ሰውየው አልተለቀቀምና፡፡ የሄዱት ሌላ ቦታ ነበር)  
- ቢመጡልን ጥሩ ነበር ስንል መጡ አይደል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ነገሩን ለማወቅ ስለፈለግሁ ነው እንጂ በዚህ ሰዓት እዚህ ቦታ መገኘት አልነበረብኝም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር የኒውዮርክ ገዢ ከሴተኛ አዳሪዎች ጋር ይገናኝ እንደነበር ዛሬ ይፋ ተደረገ፡፡ ይቅርታ ጠየቁ፣ በቃ፡፡ እርስዎ ከእኛ ለአገርና ለወገን ከሚያስቡ ባለሃብቶች ጋር መገናኘትም ምን የሚያሳፍር ነገር አለው ያኮራል እንጂ፡፡
- እኔ ያሳፍራል አላልኩም፡፡ መሽቷል ነው ያልኩት፡፡
- ብቻ ወደቁም ነገሩ እንግባ ክቡር ሚኒስትር፡፡ በጥሞና ያዳምጡን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እሺ አዳምጣለሁ፡፡
- ይኸውልዎት እርስዎን እንደ አባት፣ እንደወንድም ነው የምናይዎት፡፡ እንደ ባለስልጣን አይደለም፡፡ ባለሃብቱን ለማሸሽ ወርቅ፣ ባንክ እየተባለ መወንጀል ተጀምሯል፡፡ እኛ እንኳን ልንሰርቅ ያለንን ተካፍለን እንደምንበላ ከእርስዎ በላይ ምስክር የለም፡፡
- አውቃለሁ፡፡
- የእርስዎን ቤት የሰራነውና መኪና ለባለቤትዎ የሰጠነው ሃብትና ገንዘብ ተርፎን አይደለም፡፡ እግዚአብሄር ያላችሁን ተካፍላችሁ ብሉ ስላለ ነው፡፡
- አውቃለሁ፡፡ ይህን ስለማውቅ አይደለም ወይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ውጭ ሲሄዱ አብራችሁ እንድትሄዱ ለማድረግ የምወተውተው፡፡ በቀደም ሽልማት ሲሰጥ ለሚወስኑት ሰዎች የእናንተ ስም እንዲገባ ያደረግሁት እኔ አይደለሁም ወይ? ጥሩ ለሰራልህ ጥሩ ስራ ብሏል ፈጣሪ፡፡
- ተብሏል ግን አሁን እንደምንም ብለው ይህ የተጀመረ ምርመራ እንዲቆም ያድርጉት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እ?
- ለመርማሪውም ለአዛዡም ለሌላም ለሌላም የሚሸፈን ወጪ በእኛ ይተውት፡፡ ሌላ ሰው የለንም አሁን በቃ ቅበሩን ክቡር ሚኒስትር መረጋጋት ከሌላ ኢንቨስትመንት የለም ማለት ነው፡፡ ለዚህም ለዛም የሚያስፈልግ ወጪ ይኸውልዎት፡፡
- እኔ ምንም ወጪ የለብኝም፡፡ ገንዘብ አያስፈልገኝም፡፡ ምናልባት ለነዳጅ ይሆናል እሺ፡፡
- በቃ የራሳችን የቤተሰባችን ሕይወት በእርስዎ እጅ ነው፡፡ ሌላ የምንለው የለንም፡፡
- እሺ ቻው፡፡
(ክቡር ሚኒስትሩ ቤታቸው ገቡ፡፡ ከሚስታቸው ጋር ያወራሉ፡፡ ነገር ግን ሃሳባቸው ሌላ ጋር ነው)
- ስማኝ እንጂ ምን እያሰብህ ነው? ልብህ እኔ ጋር የለም፡፡
- እየሰማሁ ነኝ፡፡ እሺ የጥሎሽ ነገር እያወራሽ ነው አይደል፡፡
- አዎን እኮ ልጨርስልህ ለጥሎሽ ወርቅ ይዘው መጡ፡፡
- እሺ፡፡
-  ቤተሰቧ የተደሰተ መሰለህ?
- ወርቅ ሲመጣ እንዴት አልተደሰቱም?
- የዘመኑ በሽታ ነዋ..
- ኤች.አይ.ቪ/ኤድስ ደግሞ ከጥሎሽ ጋር ምን አገናኘው?
- ኤድስ ማን አለህ?
- የዘመኑ በሽታ ብለሽ የለ፡፡
- ባሌስትራ ማለት ነው፡፡ የጥሎሽ ወርቅ ባሌስትራ ቢሆንስ ብለው አልጠረጠሩም መሰለህ፡፡
- ስትስቂ ነዋ የዋልሽው?
- በእናትህ የዛ ወዳጃችን አባት ሞተውኮ ቀብርም ሄጀ ነበር፡፡ እየሰማኸኝ ነው?
- ኧረ እየሰማሁ ነው ስለቀብር አይደል የምታወሪ ያለሽው፡፡
- አዎን ስለቀብር ነው፡፡
- ቀብር እንዴት ነበር?
- ምን ልበልህ... ቀብር ብሎ ዝም ነው፡፡
- አስፕሪን አለሽ ራሴን አመመኝ፡፡
- የሚዋጠውን ላምጣልህ የሚበጠበጠውን?
- ካልበጠበጠኝ የተበጠበጠውን አምጭልኝ፡፡
- ሆስፒታል ልውሰድህ?
- ለምን?
- በጭራሽ ደህና አትመስልም?
- ሥራ በዝቶብኝ ነው፡፡
- የራስህ ጥፋት ነዋ..
- ምን ጥፋት አለኝ?
- እነዛ ወዳጆችህ ገንዘብ ማቋቋሚያ እንሰጥሃለን የግል ሥራ ትጀምራለህ ብለውህ የለ ለምን እሺ አትላቸውም?
- አልገባኝም?
- መንግሥት ካባረረህ እናግዝሃለን ነው ያሉት እንጂ አሁን ከወጣሁማ ምንስ እጠቅማቸዋለሁ፡፡ እዛ ሆነህ ጥቀመን እኛም እንጠቅምሃለን ነው የሚሉት፡፡ ከቦታየ ከተነሳሁ ዞር ብለውም አያዩኝም፡፡ ብር ከሌለኝ ብወጣ ምን ዋጋ አለው?
- ኧረ ይህ ብር የሚባል ነገር የውሸት ብር ያሳተሙ ተያዙ አሉ፡፡ መረሸን ነበር የት አባታቸውንስ፡፡
- ኧረ ተው ሆስፒታል እንሂድ ፊትህ ጥሩ አይደለም፡፡
- በቃ ልተኛ አሁን፡፡

(ጧት ተነስተው የሄዱት ሆስፒታል አይደለም፡፡ ቢሮም አይደለም)
- ክቡር ሚኒስትር በጧት መጡ አይደል፡፡
- አዎን ላነጋግርህ ብዬ ነው፡፡
- ምን ችግር አለ?
- በወርቅ ጉዳይ፣ በልማት ባንኩ ጉዳይ፣ በብሄራዊ ባንክ ጉዳይ፣ ብር ያሳትማሉ፣ የሚል ወሬ አለ፡፡ ልማታችንን ለማደናቀፍ ሆን ተብሎ የሚሰራ አሻጥር እንዳይሆን ብዬ ነው፡፡ ጥርጣሬ ነው፡፡
- ውሸት አይመስለኝም፡፡ መዓት ማስረጃ እየተያዘ ነው፡፡ እኔም እንደርስዎ እንዳይሆን ሰግቼ ነበር፡፡ ግን የተረጋገጠ ነው፡፡
- እንደዚህ ዓይነት ሰዎች እንዳናጣቸው ብዬ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ግብር በመክፈል የታወቁ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ተሸላሚዎች ናቸው፡፡ ከክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ዓለምን ይዞራሉ፡፡ ጥሩዎች ባይሆኑ ይህን ሁሉ ያደርጉ ነበር ወይ?
- ብቻ ነገሩ ብዙ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡ ሰዎቹ አደገኞች ናቸው፡፡
- አደገኞች ከሆኑ አደጋ እንዳያደርሱ በትዕግሥትና በጥበብ መያዝ ነዋ..
- እኮ በትዕግሥትና በጥበብ ስለያዝነው እንጂ አንዳንድ የሚተባበሩዋቸው ባለሥልጣኖች እንዳሉ ጥቆማ ደርሶንም ነበር፡፡ ለመያዝ አልፈለግንም፡፡ በትዕግሥት ነው የያዝነው፡፡
- ሻይ ወይስ ቡና? ክቡር ሚኒስትር፡፡ የዚህን ሆቴል ቡና እወደዋለሁ፡፡
- እሺ ቡና ጥቁር ቡና እነማን ናቸው እነዚህ ባለሥልጣናት?
- ስማቸው እስካሁን አልተነገረም፡፡ ነገር ግን ማታ ማታም ቢሆን ይገናኛሉ ነው የሚባለው፡፡
- ባለሥልጣናት ካሉ በፍላጎታቸው አግባብቶ ስልጣን እንዲለቁ ማድረግ ነው፡፡ በሀገር ቀልድ የለም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ባለሥልጣን ካሉማ መረሸን ነው እንጂ የምን ስልጣን እንዲለቁ ማድረግ፡፡ በሚሊዮን ሰርተው ስልጣን ቢለቁ ምን ይጎዳል? ለሌላው ትምህርት እንዲሆን መቀጣጫ መሆን አለባቸው፡፡
- እንግዲህ በዚህ ጉዳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የካቢኔ ስብሰባ ይጠሩ ይሆናል፡፡
- ትናንትና ማታኮ አስቸኳይ ስብሰባ ጠርተው ነበር፡፡ እሱማ ግማሽ ሌሊት ነበር ስብሰባው አሉ፡፡
- የአንድ ወዳጃችን አባት ሞተው ሌሊቱን እዛ ነበርኩ፡፡ ቀን ቀብር ነበር፡፡ ሃዘን ስለሆነ ሞባይሌን አጥፍቸው ነበር፡፡  የምረዳው ካለ እንድትነግረኝ ነው፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ካለ እናገራለሁ፡፡ አሁን ልሂድ የሚያዙ ተጨማሪ ሰዎች አሉ፡፡
- በጥዋቱ ነው የምታስሩት?
- ክቡር ሚኒስትር ትናንት ልንይዛቸው ነበር፡፡ ማታ አካባቢ አንድ ባር ውስጥ ተሰብስበው ነበር፡፡ ምክንያቱን አላውቅም እንዳትይዙዋቸው ተባልን፡፡
- ለምን?
- ምናልባት በመሃላቸው ሊያዝ ያልተፈለገ ሰው አለ ወይም እሱ እያለ ግርግር መፍጠር አልተፈለገም መሰለኝ፡፡
- ማን ነው እሱ?
- ክቡር ሚኒስትር አለቆቻችን ናቸው የሚያውቁት እኛ አናውቀውም፡፡
- እነማን እንደሆኑ ስታውቅ ትነገረኛለህ?
- ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር አንድ የሬዲዮ መልዕክት መጣብኝ፡፡

(ሰውየው ለ45 ደቂቃ የሚሆን በሬዲዮ ይነጋገራል፣ ይጨቃጨቃል፡፡ ስሜታዊ ሆኗል፡፡ ይቆጣል፡፡ ከ45 ደቂቃ በኋላ ወደ ክቡር ሚኒስትሩ መጣ)
- አልሰማኸኝም መሰለኝ እነማን እንደሆኑ ስታውቅ ትነግረኛለህ?
- ምን እነማን እንደሆኑ?
- የሚፈለጉት ባለሥልጣናት እነማን እንደሆኑ ስታውቅ ትነግረኛለህ፡፡
- አወቅኩ እኮ አሁን በሬዲዮ መልዕክት ነገሩኝ፡፡
- ንገረኛ እነማን ናቸው?
- እንሂድ እዛ ወንጀል ምርመራ ክፍል ይነገርዎታል፡፡
- ምን?
- እንሂድ!!
 
< Prev   Next >