| የአደይ አበባ ድርና ማግ ፋብሪካ... |
|
|
| Wednesday, 19 March 2008 | |
|
የአደይ አበባ ድርና ማግ ፋብሪካ አመራርና የሰራተኛ ማህበሩ እየተወዛገቡ ነው
የአደይ አበባ የድርና ማግ አክሲዮን ማህበር የአመራር አካላትና የሠራተኛ ማህበሩ በፋብሪካው ህልውና ላይ ተወዛገቡ፡፡ የአክሲዮን ማህበሩ የሠራተኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ በቀለ ላየሁ ፋብሪካው ከሰባ ሚሊዮን ብር በላይ እዳ ውስጥ መዘፈቁን ጠቅሰው የፋብሪካው አመራር የገቢ ምንጭ ለማፈላለግ በሚል ሰበብ የፋብሪካውን ግማሽ አካል ለሌላ ወገን ለማከራየት ጥረት መጀመሩን ገልፀዋል፡፡ አቶ በቀለ አመራሩ በተለምዶ ቁጥር ሁለት የሚባለውን የፋብሪካውን ክፍል ለማከራየት መነሳሳቱ ከፋብሪካው ተልዕኮ ውጪ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሊቀመንበሩ በቁጥር ሁለት ፋብሪካው ውስጥ ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ዝርጋታ መከናወኑን ገልፀው፤ አመራሩ የፋብሪካውን ህልውና በሚጐዳ ሁኔታ የኤሌክትሪክ ዝርጋታውን የማፈራረስ ሥራ መጀመሩንና ፋብሪካውን ለሌላ ወገን ለማከራየት መዘጋጀቱን አስታውቀዋል፡፡ የአመራሩን የማከራየት ሀሳብ በመቃወም ባለፈው አርብ ዕለት የፋብሪካው ሠራተኞች የተቃውሞ ሰልፍ ፋብሪካው ቅጥር ግቢ ውስጥ ማድረጋቸውን አቶ በቀለ ገልፀዋል፡፡ “አመራሩ ሰራተኛ ማህበሩን ሳያማክር ብቻውን የማከራየት መብት የለውም” ሲሉ ሊቀመንበሩ አስታውቀዋል፡፡ የፋብሪካው አመራር ሰራተኛውን ለቅነሳ የማመቻቸት ሥራ እየሰራ መሆኑን አቶ በቀለ ገልፀዋል፡፡ “አመራሩ ፋብሪካውን ግማሽ አከራይቶ ህልውናውን ለማቆየት ጥረት ከማድረግ ይልቅ የገበያ ማፈላለግ ሥራ ቢሰራ የተሻለ ነው” ሲሉ ሊቀመንበሩ አብራርተዋል፡፡ የፋብሪካውን ህልውና ከማቆየት አንፃር ሰራተኛው በየዓመቱ ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ የትራንስፖርትና የደንብ ልብስ ወጪ መቀነሱን አቶ በቀለ ጠቁመው አመራሩ ከሠራተኛው አመለካከት ውጪ ፋብሪካውን እየገደለ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ የሰራተኛ ማህበሩን አቤቱታ በተመለከተ የአክሲዮን ማህበሩ ሥራ አስኪያጅ አቶ መላኩ ጥላሁን “የገቢ ምንጭ ከማፈላለግ አኳያ ቁጥር 2 ፋብሪካን ማከራየት ተገቢ ነው” ብለዋል፡፡ አቶ መላኩ በቁጥር ሁለት የሚካሄደው ሥራ አነስተኛ ከመሆኑ አንፃር ፋብሪካውን ማከራየት ጠቀሜታ እንዳለው ገልፀዋል፡፡ አቶ መላኩ በቁጥር ሁለት የሚገኙ 132 ሰራተኞችን ከቁጥር አንድ ፋብሪካ ጋር ማዋሀድ የቁጥጥር ወጪን ከመቀነስና በስራ ሂደት አጋዥ መሳሪያዎችን በጋራ ከመጠቀም አኳያ ጠቀሜታው የጐላ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሥራ አስኪያጁ ፋብሪካውን የማከራየት ሀሳብን በተመለከተ ከሠራተኛ ማህበሩ ጋር ተወያይተው መስማማታቸውን ገልፀዋል፡፡ “ፋብሪካው ቢከራይ የሠራተኛውን የስራ ዋስትና አጠያያቂ አያደርግም” ብለዋል፡፡ በተሾመ ንቁ |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |