| ክቡር ሚኒስትር |
|
|
| Wednesday, 19 March 2008 | |
|
(በቤተሰብ ሰርግ ተገኝተዋል፡፡ ፊታቸውን አሳይተው ድግሱ ከተካሄደበት ትልቁ ሆቴል ውስጥ ወዳለው ባር ሄደዋል፡፡ አንድ የሚያውቃቸው ሰው አግኝተው ማውራት ጀመሩ)
- ስለ ወርቅ መጭበርበር አልሰሙም ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር? - በወርቅ ዙሪያ ችግር እንዳለማ ሰምቻለሁ፡፡ ያጭበረበሩት ሰዎች ግን ናይጄሪያዊያን ይሁኑ ሻዕቢያ አልገባኝም፡፡ - ክቡር ሚኒስትር የምን ናይጄሪያ፣ የምን ሻዕቢያ እነ እንትና እኮ ናቸው ተጠርጥረው የታሰሩት፡፡ - እነ ማን? - አንዴ ያስታውሳሉ ፎቅ ሲመረቅ የተገናኘንበት ቦታ? - አዎን አስታውሳለሁ፤ በክብር እንግድነት ጠርቶኝ ነበር፡፡ - እሱ ሰውዬ አንዱ ነው፡፡ - ባለ ፎቁ? - አዎን እሱ ራሱ፡፡ - ትቀልዳለህ? - ክቡር ሚኒስትር ምን እቀልዳለሁ፣ ተቀለደብኝ እንጂ፡፡ - እሱ ሰውዬ አሁን ነው ሃብታም የሆነው አይደል? - አሁን እንጂ አሁን አሁን በኢሕአዴግ ጊዜ፡፡ - እሱ ወርቅ አጭበረበረ ነው የምትለኝ? - ተራ ማጭበርበር እኮ አይደለም፡፡ ባሌስትራን ወርቅ ነው ብሎ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ሰርቆ አገሪቷን አከሰረ፣ መሳቂያ አደረገ፡፡ - ወይ ጣጣ.. - አንድ ደህና ነጋዴ ያለ እንዳይመስልዎት ክቡር ሚኒስትር፡፡ - እሱማ አሉ፡፡ አንድ መጥፎ ስላጋጠመ ሌላው ደህና ነጋዴ ሁሉ መሰደብ የለበትም፡፡ ሽልማት የተሰጣቸው አሉ አይደል? በኤክስፖርት ንግድ የተሸለሙ፣ በግብር መክፈል የተሸለሙ አርአያዎች አሉኮ፡፡ - ክቡር ሚኒስትር ነገሩን አላወቁትም፡፡ - እንዴት አላውቀውም? - በኤክስፖርት ተሸላሚ ከሆኑት አንዱ፣ በግብር አከፋፈልም ከተሸለሙት አንዱ ናቸው በወርቅ ማጭበርበር የታሰሩት፡፡ - ወይ ጣጣ.. በል በል ምን አሰማኸኝ፡፡ ቤቴ ልሂድ ፍቀድልኝ፡፡ - ቻው ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ቻው፡፡ (ቤት ገብተው ከባለቤታቸው ጋር ማውራት ቀጠሉ) - ወርቅ አጭበረበሩ የተባሉት እነማን እንደሆኑ ሰማሽ? - ኧረ ወርቅ ገደል ይግባ፡፡ ሰው የቸገረው ጨው፣ ድንችና ሎሚ ነው፡፡ - ጨው ደግሞ ምን ሆነ? - በኪሎ ብር ከሃምሳ የነበረው አስር ብር ሆነ፡፡ - ትቀልጂያለሽ? - አንተ ነህ የምትቀልደው፡፡ ሚኒስትር ሆነህ ነገር አለሙን አታውቅም፡፡ - እንዴት አላውቅም የጠላትን እንቅስቃሴ ቀንና ሌሊት በትኩረት እየተከታተልን ነው፡፡ - ወይ ጠላት፡፡ በዚሁ በጨው ማን እንደታሰረ አውቀሃል? - አላውቅም - ቢንያም፡፡ - ማነው ቢንያም? - የባለ ሆቴሉ ልጅ በቀደም እኛ ቤት ለለቅሶ መጥቶ የነበረው፡፡ - እሱ ሃብታም አይደለም እንዴ? - ነው እንጂ ብዙ መኪኖች አሉት፡፡ - እና በጨው ያጭበረብር ነበር ማለት ነው? - አዎን፡፡ - ወይ ጣጣ.. - ወይ ጣጣ፣ ወይ ጣጣ፣ ወይ፣ ጣጣ አትበል ሚኒስትር ነህ፡፡ አንድ ነገር አድርግ፡፡ - ይኸው እየተለቀሙ አይደለም እንዴ? - አዎን እየተለቀሙ ናቸው፡፡ ግን በዚህ ይለቀማሉ በዚያ ይፈለፈላሉ፡፡ - ምን አይተሽ ነው? - የጨው አጭበርባሪ ታሰረ ሲባል ጨው ቀነሰ፡፡ ግን ጤፍ በኩንታል ሰባት መቶ ብር ደረሰ፡፡ - ሰባት መቶ? - አዎን፡፡ - የጤፍ ነገር እንኳ አለማወቅ፣ አለመማር ይሆናል፡፡ ኢሕአዴግ ራስህ ገበያ አውጥተህ ሽጥ ስላለው የገበያ ሁኔታ ባለማወቅ ገበሬው የሚያደርገው ይሆናል፡፡ - ወይ ገበሬ የአቶ ገብረማርያም ልጅኮ ነው ሲያጭበረብር የተያዘው፡፡ - ገብረ ማርያም ማን? - ገብረማርያም እኝህ በቀደም ቤታቸው ተመለሰላቸው ያልኸኝ፡፡ - ወይ ጣ... ጣ... - በይ በይ እንተኛ ነው፡፡ (ቢሮ ገብተዋል ክቡር ሚኒስትር፡፡ ከፀሐፊያቸው ጋር ያወራሉ) - ክቡር ሚኒስትር ጉዳይ አስፈፃሚም ተላላኪም ሆኖ ይሰራ የነበረው የእኛ ሰራተኛ ትናንት ታሰረ ብለው ከቤት ደውለው ነበር፡፡ - ለምን ታሰረ? - በጥቁር ገበያ በዶላር ምንዛሬ ይሳተፋል መሰለኝ፡፡ - እሱ ባለገንዘብ ሆኖ? - አይደለም ክቡር ሚኒስትር ይላላካል፡፡ ኮሚሽን ይሰጠዋል፡፡ - አሁን ምን አድርጉ ነው የሚሉን? - በእጁ አንድ ሚሊዮን ዶላር ስለተገኘ ሌላ አደጋ እንዳይደርስበት ክቡር ሚኒስትሩ ቢያስፈቱልን ብለው እናቱ ደውለው ነበር፡፡ - እጁ ላይ ያን ያህል ዶላር ተገኘ? - አዎን፡፡ - ወይ ጣ... ጣ.. - እኔ በእንደዚህ ዓይነት ጉዳይ ውስጥ እንደማልገባ ታውቂያለሽ? - አውቃለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡ ዛሬ ቢሮ አይገቡም ብዬ ነው የመለስኩላቸው፡፡ - እንደዚህ ዓይነት ነገር አይሰሩም አትያቸውም፡፡ በይ በይ ማን ነው ስሙ አማካሪውን ጥሪልኝ፡፡ (አማካሪው ተጠርቶ ገባ) - ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ጤና ይስጥልኝ፡፡ እባክህ የምሰማው ወሬ ሁሉ የሚያስጠላ ስለሆነብኝ ስለፕሮጀክታችን ደህና ወሬ ካለህ ንገረኝ፡፡ - ክቡር ሚኒስትር ቆመኮ፡፡ - ለምን ይቆማል? - ክቡር ሚኒስትር ሌላ ምክንያት የለውም፡፡ የሲሚንቶ እጥረት ነው፡፡ - ለሌላው ያጥራል እንጂ እኛ ከሙገር አይደለም እንዴ የምንጠቀመው? - የሙገር ነው ግን እሱም ሰላሳ ብር ጨምሯል፡፡ - እንዴ ክቡር ሚኒስትር ዛሬኮ 260 ብር ደረሰ፡፡ - ለምን? - ሲሚንቶ ማስገባት ተከለከለ፡፡ - ወይ ጣጣ... ለምን ተከለከለ? - ሲሚንቶ እንዲገባ ተፈቅዶ የነበረው ውጭ ገንዘብ አለኝ ለሚል ነበር፡፡ በፍራንኮ ቫሉታ ማለት ነው፡፡ - ምን ሆነ ታዲያ? - ከውጭ ገንዘብ ሳይኖራችው እዚህ በጥቁር ገበያ እየመነዘሩ ገንዘብ የሚልኩና የሚገዙ ሆነው ስለተገኙና የውጭ ምንዛሬውን ስላሟጠቱት ተከለከሉ፡፡ - ከዚህ በጥቁር ገበያ እየመነዘሩ ነበር ሲገዙ የነበሩት? - አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ሕንዶች ይሆናሉ፡፡ - የምን ሕንዶች ኢትዮጵያዊያን እንጂ፡፡ እዚህ እኛ የዕቃ ግዥ ኃላፊ የነበረው በገዛ ፈቃዱ የለቀቀውን ያውቁታል? - አዎን.. - ክቡር ሚኒስትር የእነሱ ናቸው፡፡እንዲያውም እሱ ታስሯል፡፡ ቀንደኛ ነው አሉ፡፡ - ወይ ጣጣ.. ጣጣ (ሂድ ፀሐፊዋን ጥራልኝ) - አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡ - ትንሽ ራሴን ስላመመኝ ቤት ሄጄ ልተኛ፡፡ - እንዴ አሁንኮ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ተደውሎ አስቸኳይ ስብሰባ አለ ተብሏል፡፡ - ስንት ሰዓት? - አሁን አሁን ይምጡ ነው ያሉኝ፡፡ (ክቡር ሚኒስትሩ ከሰዓት በፊት እዚያው ስብሰባ ላይ ዋሉ፡፡ ከሰዓት በኋላ ስብሰባው ሲቀጥል የታሸገ ፖስታ ደብዳቤ ደረሳቸው፡፡ ከፍተው አነበቡት) - ወይ ጣ... ጣ.... - ምንም አይደለም ክቡር ሚኒስትር መበርታት ነው፡፡ - መበርታትማ እበረታለሁ፡፡ ነገር ግን እኔኮ ሁሉም የሚያውቀኝ ንፁህ ሰው ነኝ፡፡ - ትክክል ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡ እርስዎን ሰረቁ፣ ጉቦ ተቀበሉ፣ ዋሹ የሚል አንድም ሰው የለም፡፡ - ታዲያ ለምን ከሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ተነስተህ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ አማካሪ ትሆናለህ የሚል ደብዳቤ ደረሰኝ፡፡ - እሱም ቢሆን ስለሰረቁ፣ ስለዋሹ ጉቦ ስለተቀበሉ አይደለም፡፡ - ታዲያ ምን አድርጌ ነው? - መወሰን አይችልም፣ እርምጃ አይወስድም፣ ጠንካራ አቋምና እምነት የለውም ተብለው ነው፡፡ - ወይ ጣ... ጣ.. - እና አሁን ስብሰባ እገባለሁ? አልገባም? እረፍት ያድርጉ ነው ያለኝ፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት እዚህ እኛ አካባቢ ሥራ ይጀምራሉ፡፡ - እሺ ቤት ልሂድ ቻው፡፡ - ደህና ይሁኑ ክቡር ሚኒስትር፡፡ (ቤታቸው ገቡ) - ምን ሆነህ ነው ፊትህ ጠቋቆረ? - ዛሬ ደስ አላለኝም፡፡ - የኃይሉን መታሰር ሰማህ እንዴ? - ማን ነው ኃይሉ? - ብሄራዊ ባንክ የሚሰራው ዘመዳችን፡፡ - አልሰማሁም ምን አደረገ ተባለ? - አዲስ ብር አላስረከብህም፣ የሚሰራ ብር አቃጠልክ፣ ብለው ነው፡፡ - ወይ ጣ... ጣ... - አንተ ደግሞ ሁሌ ወይ ጣጣ ነው፡፡ ምን ሆነህ ነው? - ስራ እየቀየርኩ ነኝ፡፡ - ምን የሚሉት መቀየር? - በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ አማካሪ ሆነህ ስራ ተብያለሁ፡፡ - ታዲያ ጥሩ ነዋ፡፡ እድገት እኮ ነው፡፡ - ከሚኒስትርነት አማካሪ ሆኖ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ መግባት እድገት ነው ብለሽ ነው? - ማስታወቂያ ሚኒስቴር የነበሩት አማካሪ ተብለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋ ናቸው፡፡ እድገት ነው? - እኔ እንጃ እስቲ እናያለን፡፡ - በቃል ነው የነገሩህ በደብዳቤ? - ደብዳቤማ ሰጥተውኛል፡፡ - እስቲ አሳየኝ፡፡ (ተሰጣቸው አነበቡት) - ወይ ጣ... ጣ... - አንቺም ወይ ጣጣ ማለት ጀመርሽ ምን ሆነሽ ነው? - ደብዳቤውን በደንብ አይተኸዋል? - አዎን ሳነበው እድገት አይደለም፡፡ - እንዴት? - አማካሪ ሆነው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ እንዲሰሩ ብቻ ነው የሚለው፡፡ - እና ምን ጎደለው? - የጎደለውማ በሚኒስትር ደረጃ አይልም፡፡ ዝም ብሎ አማካሪ ብቻ ነው የሚለው፡፡ - እስቲ ስጭኝ እንደገና ላንብበው፡፡ (ክቡር ሚኒስትሩ ደጋግመው አነበቡት) - እ.. አነበብከው በሚኒስትር ደረጃ አይልም? - ወይ ጣ... ጣ... |
| < Prev | Next > |
|---|
| Home |
| Sections |
| Forums |
| Reporter - English Ver. |
| Register |
| Contact Us |