ሙሉ በሙሉ በቻይና መንግሥት ወጪና በቻይናውያን ባለሙያዎች የተገነባው ባለ28 ፎቅ የአፍሪካ ኅብረት ዋና መሥርያ ቤት አዲሱ ሕንፃ፣ በመጪው ቅዳሜ ከፍተኛ የቻይና ባለሥልጣናትና የአፍሪካ መሪዎች በሚገኙበት ሥነ ሥርዓት ይመረቃል፡፡
ለሕንፃው ግንባታ ከ150 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ መደረጉን፣ የሕንፃውን የምረቃ ሥነ ሥርዓትና ቀጣዩን የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ አስመልክቶ በትናንትናው ዕለት ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የአፍሪካ ኅብረት ተወካዮች ገልጸዋል፡፡ የግንባታው ወጪ ሙሉ በሙሉ በቻይና መንግሥት የተሸፈነ መሆኑን ያብራሩት ተወካዮቹ፣ ይህም የቻይናንና የአፍሪካን ወዳጅነት የበለጠ ለማጠናከር በቻይና መንግሥት የተወሰደ ዕርምጃ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በተጨማሪም የሕንፃ ግንባታው ፕሮጀክት የቻይና አፍሪካ መድረክ የጋራ ስምምነት አካል መሆኑን ተወካዮቹ አብራርተዋል፡፡ በ110 ሺሕ ካሬ ሜትር ላይ ከተገነባው ሕንፃ ምረቃ ሥነ ሥርዓት በኋላም፣ የወቅቱ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ዦን ፒንግ ቁልፉን ይረከባሉ ተብሏል፡፡
በዚሁ የምረቃ ሥነ ሥርዓት ላይ ለመገኘትና በቀጣዩም የሚካሄደውን የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ ለመካፈል አዲስ የተመረጡት የቱኒዚያው ፕሬዝዳንት፣ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የሊቢያ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡


