በምሕረት አስቻለው
ዓይኗ ከወዲያ ወዲህ ያማትራል፡፡ ቀትር ዘጠኝ ሰዓት ቦሌ መድኃኔ ዓለም አካባቢ ነው፡፡
የምትመለከተው ከአስፋልት ግራና ቀኝ ተደርድረው የቆሙትን መኪኖች ነው፡፡ ድምፅ ስትሰማ ዞር ዞር እያለች ዙርያ ገባውን ትመለከታለች፡፡ የሚንቀሳቀስ መኪና ስታይ ሮጥ ሮጥ እያለች በመሔድ የፓርኪንግ ሒሳቧን ትቀበላለች፡፡ ወዲያው ደግሞ ከመንገድ ዳር ጥግ ላይ ወዳስተኛቸው የአሥራ አንድ ወር ልጇ ታመራለች፡፡ ሕፃኑን ካስተኛችበት ስፍራ ፀሐይ ሲያርፍ አንሥታ ጥላ ወዳጠላበት ቦታ ትወስደዋለች፡፡ ከእንቅልፉ ነቅቶ ካስቸገረም አቅፋ ወይም አዝላ ሩጫዋን ትቀጥላለች፡፡
አማረች አየነው ሃያ ሦስት ዓመቷ ቢሆንም፣ የገረጣው ፊቷና አጠቃላይ ጉስቁልናዋ ከዚያ በላይ ያስመስላታል፡፡ የተወለደችው ወላይታ ጉሩሞ ኮሻ በሚባል ቦታ ነው፡፡ ወደ አዲስ አበባ የመጣችበትን ጊዜ በትክክል ባታስታውሰውም የሰባት ዓመት ሕፃን ሳለች እንደሆነ ትገምታለች፡፡ ያመጣቻት አሳዳጊዋ ስትሆን ስለ ወላጆቿ የምታስታውሰውም፣ የምትለውም ነገር የላትም፡፡
‹‹የምንኖረው ኮተቤ አካባቢ ነበር፡፡ የአሳዳጊዬን ሦስት መንታ ልጆች አሳድጌያለሁ፡፡ መማር ብፈልግም አላስተማረችኝም፡፡ በጭቆና ነው የኖርኩት፡፡ እዚህም ሆነ ክፍለ አገር የኔ የምለው ሰው ስለሌለኝ ከችግር ውስጥ ነበርኩኝ፡፡››
የምትኖርበት ሁኔታ አለመመቸት ልትቋቋመው ከምትችለው በላይ ስለነበር የአሳዳጊዋን ቤት ጥላ ወጣች፡፡ ስትወጣም ይሔ ጥሩ ያ መጥፎ ብላ ሥራ ሳትመርጥ ልትሠራ ወስና ነው፡፡ በዚያ መሠረትም ቀንና ሌት መልፋቱን ተያያዘችው፡፡ የሕይወት ውጣ ውረድ ግን በቀላሉ የሚገፋ አልሆነም፡፡ ሁለት ጊዜ ከጎዳና ላይ ወጥታለች፡፡ ማደርያ አጥታ እንዲያስጠጓት በተለያዩ ሰዎች ቤት ተንከራትታለች፡፡ ይኽ ሁሉ ሲሆን ግን ከአሳዳጊዋ ቤት እንደወጣች የጀመረችውን የፓርኪንግ ሥራ አላቋረጠችም፡፡ ዘወትር በሥራ ገበታዋ ላይ ትገኛለች፡፡
‹‹ቀን እየሠራሁ በቤተ ክርስቲያን ደጃፍ በማድርበት ወቅት አንድ አብሮኝ የሚሠራ ሰው እሱ ቤት ተጠግቼ እንድኖርና ሊረዳኝ እንደሚችል ነገረኝ፤›› የምትለው አማረች፣ የሥራ ባልደረባዋ ባለትዳር በመሆኑ እሱ ስለፈቀደ ብቻ ከቤቱ ተጠግታ መኖር እንደማትችል ስለተሰማት የሚስትየውንም ፍቃደኛ መሆን አጣራች፡፡ የሥራ ባልደረባዋ ባለቤትም ልታስጠጋት በመፍቀዷ ከቤታቸው ገባች፡፡
ለቤት ኪራይ ወይም ለዚህ ነገር ተብሎ የምትጠየቀው ገንዘብ ባይኖርም አቅሟ በፈቀደ መጠን ለተለያዩ የቤት አስቤዛዎች ገንዘብ ወጪ ታደርጋለች፡፡ በዚህ ቤትም የአማረች ቆይታ ቀላል አልሆነም፡፡
‹‹የሥራ ባልደረባዬ ሚስት ሥራዋ ሌሊት ሌሊት በመሆኑ ዘወትር ከቤት አታድርም፡፡ የምናድረው እኔ፣ እሱና የሚያሳድጓት አንዲት ሴት ልጅ ናት፡፡ እሱ ብዙ ጊዜ ያስቸግረኝ ስለነበር በፍርሀት ሐሳቡን ለማስቀየር በደሜ ውስጥ የኤች አይ ቪ ቫይረስ እንዳለ እነግረው ነበር፡፡ እሱ ግን እሺ አላለም፡፡ በአንድ ሌሊት ደፈረኝ፡፡ በዚያች ምሽት ግንኙነት አረገዝኩ፤›› በማለት የስድስት ወር የዚያ ቤት ቆይታዋ ሕይወቷን ይበልጥ እንዳወሳሰበው ትናገራለች፡፡
ወልዳ ከቤት እስከዋለችበት ቀን ድረስ ሥራ አላቋረጠችም ነበር፡፡ እርግዝናዋ ከባድ የነበረ ቢሆንም ከመሥራት ውጭ ምርጫ አልነበራትም፡፡ አራስ ቤትም ብዙ አልቆየችም፡፡ ልጇ አንድ ወር ሲሞላው ወደ ሥራዋ ተመለሰች፡፡ ጊዜው ክረምት በመሆኑ የአንድ ወር አራስ ሕፃን መሬት ላይ ማስተኛት ከባድ ስለሆነባት ፓርኪንግ የምትሠራው አዝላው ነበር፡፡ አንዳንዶች ሥራ እየሠራች ሳይሆን ለልመና ወዲያ ወዲህ የምትል ይመስላቸው ነበር፡፡ ሌሎች ደግሞ ለመሥራት ያላትን ቁርጠኝነትና ጥንካሬ አድንቀው በተለያየ መንገድ ረድተዋታል፡፡ ከረዷት ሰዎች መካከል አንደኛዋ ለልጇ ወተት የተከራዩላት ሲሆን እስከ ዛሬም ድረስ ዕርዳታቸውን አላቋረጡም፡፡ ልጇ ብዙም ሰው የማይቀርብ ዓይነት ቢሆንም በምታስተኛበት አካባቢ የሚገኙ የንግድ ቤት ሠራተኞች አንዳንዴ እንደሚያጫውቱላትና ሥራ ሲበዛባትም በዓይን እንደሚከታተሉት አውግታናለች፡፡
ከጧቱ አንድ ሰዓት ከቤት ወጥታ እስከ ምሽቱ አንድ ሰዓት ስትሠራ ትውላለች፡፡ ከወተት ጋር ቀላቅላ ያፈላችውን አጥሚትም ለልጇ ስትመግብ ትውላለች፡፡ ምንም እንኳ ልጇ የሚውለው ጎዳና፣ የሚተኛውም አስፋልት ዳር ካርቶን ተነጥፎ ቢሆን በቀን ሁለት ሦስት ጊዜ ልብስ ይቀየርለታል፡፡ ፋታ በምታገኝበት ክፍተትም ታጠባዋለች፡፡ ለሷ ግን በመንገድ ላይ ሻይ ከሚያዞሩ የሚቀማመስ ገዝታ ጎርሳ ትውላለች፡፡ ጦም ውሎ አድሮ መሥራትም ለሷ እንግዳ አይደለም፡፡
‹‹አንዳንዴ በወር አራት ወይም አምስት መቶ ብር አገኛለሁ፤ ለቤት ኪራይ ሁለት መቶ ብር እከፍላለሁ፡፡ ትልቁ ጭንቀቴ ልጄና የቤት ኪራይ ነው፤›› ትላለች፡፡


