በመሠረት ከበደ
እናቶች ሴቶች ልጆቻቸውን ለምን ሁሌም ከልባቸው ይንከባከቡናል? ሴቶች ልጆቻቸውስ በተለይ ከተወሰነ ዓመት በኋላ እናቶቻችንን ለምን እንወዳቸዋለን? ‹‹ሌዲስ ሆም ጆርናል›› የተባለ መጽሔት ያወጣውን የአንዲት ሴት ጽሑፍ ኢንተርኔት አሠራጭቶታል፡፡
አሁን አሁን ለእናቴ ጠዋት ጠዋት ስልክ እደውልላታለሁ፡፡ የምደውልላት ቤት ውስጥ፣ ልጆቹን ከእንቅልፋቸው ከቀሰቀስኩ፣ ዕቃ ካጣጠብኩ፣ ቁርስ ከሠራሁና ከተበላ በኋላ ወይም ምሳ ሳህናቸውን ከትቼ ወደ አውቶቡስ ጣቢያ እየወሰድኳቸው ወይም ትምህርት ቤት እያደረስኳቸው ሊሆንም ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ መሥሪያ ቤት ገብቼ ሥራዬ እየሠራሁ ሊሆን ይችላል፡፡
ከሁሉም የሚገርመኝ ደግሞ ሁሌም ስደውልላትና ስልኩን አንስታ ድምፄን ስትሰማ ድምጿ ደስተኛነቷን ማንፀባረቁ ነው፡፡ ዘወትር መደዋወል የጀመርነው ከሦስት ዓመት በፊት ነው፡፡ አባቴ ከሞተ በኋላ ደውዬ የምነግራት ስለራሴና ስለቤተሰቤ ነው፡፡ በዚህ ምድር ላይ ስለራሴም ይሁን ስለልጆቼ የምናገረውን ሁሉ በመስማት የእርሷን ያህል የሚደሰት ማን ይሆን? በየዕለቱ ምን እንደፈለግሁ ወይም ላደርግ እንደሆነ እዘረዝርላታለሁ፡፡ ስለልጆቼም እነግራታለሁ፡፡
በዚህ በሁለታችን ዓለም ውስጥ የማይረባ ተብሎ የሚተው ነገር የለም፡፡ እኔና እናቴ ታዲያ ምን እያደረግን ነው? ግንኙነታችንን እየጠበቅን፣ ሁሉ ነገር መልካም እንደነበረ መረጃ እየተለዋወጥን? ወይስ ምን?… ምንም ብትሆን ሁሌም እናቴ ናት፣ ምንም ብትሆን ሁሌም ልጇ ነኝ፡፡ ግን ሁለታችን አዋቂዎች፣ ሁለታችንም ራሳችንን የቻልን ብንሆንም ጓደኞች እየሆንን ነው፡፡
ወጣት በነበርኩበት ጊዜ ያን ሁለታችን አንድ ቤት በምንኖርበት ጊዜ ግንኙነታችን ችግር ነበረበት፡፡ እናቴ ከእንቅልፌ ትቀሰቅሰኝ ነበር፡፡
‹‹ሴት ልጆች ወደ አዋቂነት ደረጃ በሚሸጋገሩበት የኮረዳነት ጊዜ በእናትና በልጆች መካከል ያለው ግንኙነት እናቶችን ለከባድ ኃላፊነት ያጋልጣል፡፡ የእናቶች ጤና አሳሳቢ እየሆነ በሚሄድ ጊዜ ቅርርባቸው የሴት ልጆችን ኃላፊነት ያከብዳል፤›› ይላሉ፡፡ ኢንዲያና በሚገኘው የፓርዱ ዩኒቨርሲቲ በሰው ልጅ ዕድገትና ቤተሰብ ላይ ጥልቅ ጥናት ያደረጉት ከረን ፊንግማን (ዶ/ር)፡፡
እኒህ ምሁር በአረጋውያን እናቶችና በአዋቂ ልጆች መካከል ባለግንኙነት ላይ የሚያተኩር መጽሐፍ ጽፈዋል፡፡ ‹‹በልጆች የኮረዳነት ጊዜና በእናቶች የእርግዝና ዘመን መካከል ባለው የሁለቱ የግንኙነት ዘመን ያለው የስሜት መቀራረብ ከፍተኛ ሥፍራ ላይ የሚደርስበት ወቅት ነው፡፡ ሆኖም ግን የእያንዳንዳቸውን ደካማ ጎን ለመቀበልም ትንሽ ችግር ይኖራል፡፡ ይህ ዘመን በስሜት የተሞላ ነው፡፡ ምንም ጉድለት በእያንዳንዳቸው ውስጥ ቢኖር ግንኙነታቸውን ሳያላላ በስሜታዊነት እንዲቀራረቡ ያደርጋል፤›› ብለው ስለእናትና ሴት ልጇ ወይም ሴት ልጆችዋ ግንኙነት ጽፈዋል፡፡
ይህ ዓይነቱ መግባባትና መተሳሰብ በከፊል በቀድሞ ጊዜ የነበራቸው ሻካራ ግንኙነት ውጤት መሆኑን የእኚሁ ዶክተርና የሥራ ባልደረባቸው (ረዳት ፕሮፌሰሯ ኢቫ ሌፍዊትዝ) ጥናት ያመለክታል፡፡ ጥናቱ የተካሄደው ጀ2001 ነው፡፡ በዚህ ጥናታቸው በ69 እና 93 ዓመት መካከል ያሉ 46 እናቶችንና በመካከለኛ ዕድሜ ማለትም ከ32 እስከ 60 ባለው የሚገኙ ሴት ልጆቻቸውን አካቷል፡፡ እናትና ልጅ ያሉበት ፎቶግራፍ ተሰጣቸውና እናትና ልጆቹ ስለፎቶግራፍ እንዲጽፉ ተደረገ፡፡
ታሪኩን በተለያየ ሁኔታና መንገድ ቢጽፉትም ግንኙነታቸው ጥሩ ነው፡፡ አንዳንዶቹ ልጆች ታሪኩን ለብቻቸው ጽፈው ሰጥተዋል፣ ሌሎች ደግሞ እናቶቹ እንዲጽፉ አድርገዋል፡፡ የተቀሩት ተጋግዘው ጽፈዋል፡፡ በመካከለኛው የነበረውን መጥፎ ስሜት ከአንድ እስከ አምስት በመዘርዘር ተመራማሪዎቹ አማካዩን አውጥተው ነበር፡፡ 1.2 የእናቶች፣ 1.3 ደግሞ የልጆች ሆኖ ቀርቧል፡፡ ይህንን በቃላት ሲዘረዝሩት እንዲህ ብለዋል፡፡
‹‹በመካከለኛው ዕድሜ ያሉ ሴቶች ከወጣት ሴቶች በበለጠ ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ በወጣትነት አብረው የሚሆኑ ጊዜ ኮረዶች ሳይሆኑ እናቶቻቸው ናቸው የንግግሩን መድረክ የሚቆጣጠሩት›› ይላሉ (ዶ/ር) ሌፍኮዊትዝ፡፡ ‹‹የንግግሩን መድረክ ቢቆጣጠሩም ግን በመካከለኛ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሴቶች እናቶቻቸው እንዲናገሩ ይገፋፋሉ፣ ያደፋፍራሉ፡፡››
ከእናቱ ጋር ስለነበረኝ ግንኙነት ሳስብ ሁኔታው አያስገርመኝም፡፡ ወጣት ሳለሁ ትንሽ ዋልጌነት ያጠቃኝ ነበር፡፡ ‹‹እንደምን አደርሽ›› ስትለኝ እንኳን ጥርሴን ነክሼ በንዴት ነበር ‹‹እንዴት አደርሽ ውዴ!›› እላት የነበረው፡፡ ከልብ በመነጨ የእናትነት ስሜት ‹‹ለምን እንዲህ ትሆኛለሽ?›› ስትለኝ መልሴ ‹‹አትጨቅጭቂኝ!›› የሚልና በጩኸት የተመላ ነበር፡፡ ያኔ ቁጡና ተናዳጅ ነበርኩ፡፡ የእናቴን ዕርዳታ ሳልፈልግ ሁሉን ነገር ለብቻዬ የምወጣው ይመስለኝ ነበር፡፡ ይቅር ባይ በመሆኗ ‹‹አስቸጋሪ ግን ደስ የምል›› ልጅ መሆኔን ነበር የምትነግረኝ፡፡ ሁሌም ስለእኔ ማወቅ ትፈልጋለች፡፡ እኔ ግን በጩኸት ነበር መልስ የምሰጣት፡፡
ኮሌጅ ስገባ፣ ስሜቱ እየቀየረ መጣ፡፡ መጀመሪያ ኮሌጅ ያደርኩ ቀን ስልኩ በጠዋት ጮኸ፡፡ አብራኝ የምትኖረዋን ተማሪ እንዳይቀሰቅሳት ቶሎ አነሳሁት፡፡ እማዬ ነበረች፡፡ ‹‹መኝታ ቤትሽ ልቀሰቅስሽ ሄድኩ፣ አንቺ ግን የለሽም›› አለችኝ፡፡ እየሳቀች ድምጿን ለቅሶ ይተናነቀዋል፡፡ አብሬያት ብስቅም እኔም ሳግ ይተናነቀኝ ነበር፡፡ አስቸጋሪ እንቅልፋም ነኝ፡፡ እኔን መቀስቀሱ ለእሷ አድካሚ ነው፡፡ ቢሆንም ልትቀሰቅሰኝ ሄዳ ስታጣኝ ሐዘን ተሰማት፡፡ ይህ ደግሞ ለየት ያለ ነገር በመሀከላችን እንዳለ ያሳያል፡፡
ያቺ ቅጽበት ወደ በሳልነት፣ በጠብ የተሞላ የነበረውን ዘወትራዊ ሕይወቴን ወደ መርሳት፣ የእናቴን ፍቅር ወደ መገንዘብ የተሸጋገሩኩባት ናት፡፡ ከእናቴ ጋር በስልክ ስንነጋገር የክፍል ተጋሪ ጓደኛዬ ነቅታ ወደ መታጠቢያ ቤት ለመሄድ ተነሳች፡፡ በጥያቄያዊ አስተያየት ስትመለከተኝ እናቴ መሆኗን ነገርኳት፡፡ ‹‹ገባኝ›› በሚል አስተያየት አይታኝ ሄደች፡፡
ባደግሽ ቁጥር እናትሽ ብቻ ልታደርገው የምትችል ነገር እንዳለ ታውቂያለሽ፡፡ የመጀመሪያ ልጄን ስወልድ አብረውኝ የነበሩት እማዬና ባለቤቴ ብቻ ነበሩ፡፡ ማዋለጃ ክፍል እያለሁ ‹‹እንኳን እሷ ኖረች፣ እሷ ወልዳለች፣ ታውቀዋለች›› እል ነበር፡፡ የዚህ ሁሉ መጨረሻ ልጅ እንደሚሆን አመንሁ፡፡ ሰዓቱ በደረሰና ምጡ በተፋፋመ ጊዜ ባለቤቴና እናቴ ከጎኔ ነበሩ፡፡ እኔ ባለቤቴና እናቴ ወላጆችና አያት ለመሆን በቃን፡፡
ብዙዎቻችን ልጅ መውለዳችን ለእናቶቻችን ያለንን አመለካከት ፍቅር ጠንካራና ጥልቅ ያደርገዋል፡፡ ማንነታቸው ለእኛ ቀድሞ የውሸት ይመስለን የነበረውን ስሜት በግልጽ እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ ለምን እንደዚያ ይሆኑልን እንደነበር ይገባናል፡፡
‹‹እናቴ ወንድሜና እህቴ (እኔም ጭምር) እያደግንና እየጎረመሰን በመጣን ቁጥር ይሰማት የነበረውን ጭንቀት ሳይ እበሳጭ ነበር ትላለች፡፡ ቦስተን የምትኖረው ሐኪም ኤለን ኮስቴሎ፡፡ የሦስት ልጆች እናት ናት፡፡ ያኔ ወጣት ሳለች እናቷ ይነግሯት የነበሩትን ሁሉ ከግምት አታስገባም ነበር፡፡›› ልጆች ወለድኩ፣ እናት በመሆን በሚመጣው ስሜት መሰቃየት ጀመርኩ፡፡ ልጆቼ ምን ይሆኑ ይሆን? ምን ያገኛቸው ይሆን ማለት ጀመርኩ፡፡ መሆን ሲገባቸው ስላልሆኑ ነገሮች መጨነቅ ጀመርኩ፡፡ አሁን ገና ለእናቴ አዘንኩላት፤›› ብላለች፡፡
እናቶቻችን ሁሌም አብረውን እንደማይኖሩ እናውቃለን፡፡ ልክ ስናውቃቸው ትተውን ለመሄድ ይዘጋጃሉ፡፡
‹‹ከእርሷ ጋር አወራበት የነበረው ጊዜ ይናፍቀኝ ጀምሯል›› ትላለች ኤልሳቤት በርኔት፡፡ ‹‹ብዙ የምጠይቃት ጥያቄዎች አሉኝ፡፡ ሁልጊዜ እኛ ከትምህርት ቤት ስንመጣ ቤት ትጠብቂን ነበር? ወይም ልጆችሽ ስንጣላ ምን ነበር የምታደርጊው ልላት እሻለሁ…›› ትላለች፡፡
ከእናቶች ጋር ጓደኛ መሆን የማደግ ምልክት ነው፡፡ እናቶች ሁሌም እናት ናቸው፡፡ በአስቸጋሪ ሰዓት እንኳ ይንከባከቡናል፡፡ ስናድግ ደግሞ በተጨማሪ ለሌላ ጉዳይም ያስፈልጉናል፡፡ እርስ በርሳችን እንግባባለን፡፡ አንዳችን አንዳችንን እንግባባለን፣ አንዳችን አንዳችንን እናበረታታለን፡፡ መልካሙን ጊዜ እያነሳን እናወራለን፡፡ እንጫወታለን፡፡ እናቶቻችን ከጓደኛም በላይ ናቸው፡፡ ለእናቴ ደውዬ ስለራሴ ወይም ስለቤተሰቤ ስነግራት ደስታ እንደሚሰማት አውቃለሁ፡፡ ከማንም የበለጠ ለእኔ ለልጇ መልካሙን የምትመኝ ናት፡፡ ከማንም የበለጠ ባደረግኳቸው ነገሮች እንድትደሰትና ያደረግኳቸውን ነገሮች እንድትቀበለኝ የምፈልገው እናቴን ነው፡፡
በፊት የሚያደርጉትን ነገሮች አድገንም ማድረግ ይቀጥላሉ፡፡ እናቴ ቤት ስሄድ ሻይ ታፈላልኛለች፣ ምግብ ትሰጠኛለች፣ እንደ ሕፃንነቴ ትንከባከበኛለች፡፡ ስተኛ ልብስ ላዬ ላይ ትጥልብኛለች፣ አንዳንድ ሰው ቤት ስሄድ ለምን እንደ እናቴ ምግባቸው እንደማይጣፍጠኝ፣ ቤታቸውና ራሳቸውም እንደማያምሩ ግራ ይገባኛል፡፡ አንዳንዴ እንደዚህ ዓይነት ስሜት ሲሰማኝ ባፍርም ያለገደብ ከምትወደኝ እናቴ ጋር በመሆኔ ያስደስተኛል፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡