በሰሜን ኢትዮጵያ በነበረው ጦርነት በአማራና በአፋር ክልሎች ጉዳት ደርሶባቸው ከነበሩ 43 ሆስፒታሎች መካከል፣ አምስቱን በፀጥታ ሥጋት እሳከሁን ወደ ሥራ መመለስ አለመቻንሉ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
የጤና ሚኒስቴር የፖሊሲ ፕላን ክትትልና ግምገማ ዳይሬክተር አቶ ናኦድ ወንድይራድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ጉዳት ከደረሰባቸው 36 ያህል ሆስፒታሎች በከፊል አግልግሎት መስጠት ቢጀምሩም፣ ቀሪ አራት ሆስፒታች በአማራ ክልልና አንድ ሆሰፒታል በአፋር ክልል ከፀጥታ ሥጋት ባለመውጣታቸው ሥራ ማስጀመር አልተቻለም፡፡
የአማራ ክልል አደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽን በክልሉ በሕወሓት ሥር ባሉ አካባቢዎች በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች በተለይም የሐኪም ዕገዛ የሚስፈልጋቸው ነፍሰ ጡሮች፣ የስኳር፣ የደም ግፊት፣ የኩላሊትና መሰል በሽታ ተጠቂዎች በመድኃኒት ፍለጋ ወደ አጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች መፈናቀላቸውን ለሪፖርተር የተናገሩት ከአንድ ሳምንት በፊት ነበር፡፡
የጤና ሚኒስቴር ከሰሜኑ የኢትዮጵያ ጦርነት ጋር በተገናኘ በአማራና በአፋር ክልሎች ከ1,500 በላይ ጤና ተቋማት መውደማቸውና መዘረፋቸውን ይፋ ያደረገው፣ በ2014 ዓ.ም. የመጀመርያ ወራት ነበር፡፡
በተመሳሳይ ለኅብረተሰብ ጤና ወሳኝና አስፈላጊ የሆኑ መድኃኒቶችን እየተገባደደ ባለው 2014 ዓ.ም. ገዝቶ ለማቅረብ 137 በመቶ የዋጋ ንረት መታየቱን፣ ይህ ጭማሪም የሚኒስቴሩን የመግዛት አቅም በግማሽ እንደቀነሰው የጤና ሚኒስቴር የበላይ ኃላፊዎች የ2014 ዓ.ም. አሥር ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲያቀርቡ ተናግረዋል፡፡ በሪፖርቱ እንደቀረበው በአሥር ወራት ውስጥ ከ28 ቢሊዮን ብር በላይ መድኃኒትና የሕክምና መሣሪያዎች ግዥ ተካሂዷል፡፡
በዓለም ገበያ መድኃኒት ለመግዛት ከታየው ከፍተኛ የዋጋ ንረት በተጨማሪ፣ አገር ውስጥ ያሉ መድኃኒት ገዥ ተቋማት የመግዛት አቅም እየተደካመ መሆኑም በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡
በአገር ውስጥ የጤና መድኃኒትና ሕክምና መገልገያ መሣሪያ አምራቾችን በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የማምረት አቅማቸውን በቀጣዮቹ አሥር ዓመታት ወደ 60 በመቶ ከፍ ለማድረግ በሚኒስቴሩ ዕቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም፣ ከአምስት ዓመት በፊት ከነበሩበት 24 በመቶ የማምረት አቅማቸው አሁን ከአሥር በመቶ በታች መውረዱ ተነግሯል፡፡