በአማራ ክልል ደቡብ ጎንደር ዞን ፎገራ ወረዳ ከሚገኙ ማኅበረሰቦች አንዱ አውራ አምባዎች ናቸው፡፡ የአውራ አምባ ማኅበረሰብ በ1964 ዓ.ም. በዙምራ ኑሩ አስተባባሪነት በ19 ሰዎች እንደተመሠረተ ይነገራል፡፡ ዙምራ አምስት መሠረታዊ ሀብቶችን በመያዝ ማኅበረሰቡን እንደመሠረተ ይታወቃል፡፡ የሴቶች እኩልነት ማክበር፣ የሕፃናትን መብት ማክበር፣ በጤናም ሆነ በእርጅና ምክንያት ተሰናክለው ለሥራ ብቁ ያልሆኑ ሰዎች ወላጆቻቸውን ያጡ ልጆችን መንከባከብ፣ መጥፎ አነጋገርን፣ መጥፎ አሠራርን ማስወገድ (ስርቆትን፣ ሌብነትን፣ ስድብን፣ እርግማንን፣ ድብደባን፣ ግድያን ጥላቻን)፣ የተበጣጠሰ ግንኙነትን ማስወገድ የሚሉት ናቸው፡፡ ማኅበረሰቡ እነዚህንና መሰል በጎ ሥራዎቹን ከአገር አልፎ ለዓለም በማስተዋወቅ ዕውቅና ማግኘቱ ይነገራል፡፡ በዚህም ብዙዎቹ ተሞክሮዎችን ወስደው እየጠቀሙ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ በርካታ ጥናቶችና የሚዲያ ሥራዎች እየተሠሩ ቢገኝም፣ በተቀናጀ መንገድ የማኅበረሰቡን ታሪክ፣ መልካም እሴቶችና የለውጥ ሒደት በአግባቡ ሰንዶ የማስቀመጥ ውስንነቶች አሉበት፡፡ በዚህ ዓመት ማኅበረሰቡ ‹‹ኑ ጠቃሚ እሴቶቻችን በጋራ እንገንባ›› በሚል መሪ ቃል 50 ዓመታትን የሚዘክር ዝግጅት አዘጋጅቷል፡፡ የማኅበረሰቡን ሥራዎች አስመልክቶ የአስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢዋን ወ/ሮ እናነይ ክብረትን ሔለን ተስፋዬ አነጋግራቸዋለች፡፡
ሪፖርተር፡- የአውራ አምባ ማኅበረሰብ እንዴት ተመሠረተ? ዓላማውስ ምንድነው?
ወ/ሮ እናነይ፡– የአውራምባ ማኅበረሰብ የተመሠረተው በዙምራ ኑሩ አማካይነት ነው፡፡ ከጥቂት ሰዎች ጋር የመሠረቱት ማኅበረሰብ ነው፡፡ ማኅበረሰቡ አምስት ዋና ዋና መሠረታዊ ሒደቶች አሉት፡፡ እነሱም የሴቶች ሁሉን አቀፍ እኩልነት፣ በልጆችና ሕፃናት ውበትና አስተዳደግ፣ በጤናም ሆነ በእርጅና ምክንያት የተዳከሙና ለሥራ ብቁ ያልሆኑ ወገኖችንና ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን መንከባከብ፣ መጥፎ አነጋገርና አሠራር ማስወገድ፣ የዓለም የሰው ልጆች የአንድ ሐረግ ፍሬ እህትና ወንድም መሆናቸውን በማመን እያስተማረ የዘለቀ ማኅበረሰብ ነው፡፡ እነዚህን የማኅበረሰቡ እሴቶችና መርሆዎች እየተገበረ ለአምሳ ዓመታት ዘልቋል፡፡ በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ከሕፃን እስከ አዋቂ የማኅበረሰቡን እሴት በመተግበርና በመኖር (በድርጊት) ለትውልድ እያስተላለፈ ዘልቋል፡፡ ረዥሙን ጊዜ የሚያሳልፈው በሥራና ለሰዎች በጎ ነገሮችን በማድረግ ስለሆነ ጥል፣ መገፋፋትና መሰዳደብ አስወግዶ ኖሯል፡፡ ሰላምና መተሳሰብ የሰፈነበትና የሰውን ልጆች በእኩል መኖር እንዲችሉ ማድረግ ዓላማው ስለነበረ ማኅበረሰቡ በፍቅርና መተሳሰብ እየኖረ ይገኛል፡፡
ሪፖርተር፡- ማኅበረሰቡ ያለውን ተሞክሮ ለሌሎች ለማሳየትና ለማስተላለፍ ችላችኋል?
ወ/ሮ እናነይ፡– ማኅበረሰቡ እየኖረው ያለው ሰዋዊ እሴቶች በብዙዎች ተፈላጊ በመሆኑ፣ ሌሎችም የማኅበረሰቡ ክፍሎች እየተገበሩት ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ በወሎ ባቲ እና ቆቦ ላይ የሥርዓተ ፆታ እኩልነትን ከመተግበር አኳያ ብዙ እንቅስቃሴ አድርጓል፡፡ በሌላ በኩል ጎጃም አቸፈር ወረዳ ላይ ሌብነትን ከአካባቢው ለማጥፋት ችለዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ አካባቢዎች የአውራምባ ማኅበረሰብ ኢፍትሐዊነትን በማስወገድና ሌብነትን በመጸየፍ ያመጣውን ለውጥ ተመልክተው በአካባቢያቸው በመተግበራቸው እፎይታ አግኝተዋል፡፡ አሁንም ከእነዚህ አካባቢዎች በተጨማሪ በመላው ኢትዮጵያና በዓለም የማኅበረሰቡ እሴቶች እንዲተገበሩ የማድረግ ትልቅ ህልም አለን፡፡ በ1964 ዓ.ም. በዙምራ ኑሩ የተመሠረተው የአውራ አምባ ማኅበረሰብ፣ ለረዥም ዓመታት ፍርድ ቤት ሄዶ አያውቅም፡፡ ችግር ቢፈጠር እንኳን ለርሱ ተብሎ በተዘጋጀው ኮሚቴ አማካይነት በቀላሉ እንዲፈታ ስለሚደረግ፣ ለፍርድ ቤት የሚያበቃ ጉዳይ በእኛ አካባቢ ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ይቅርታ ሰሚ ኮሚቴ በማኅበረሰቡ አማካይነት ስለተመሠረተ ችግሮች በእንጭጩ እንዲቀረፉ ያደርጋሉ፡፡
ሪፖርተር፡- የአውራ አምባ ማኅበረሰብ ታሪክ፣ መልካም እሴቶችና የለውጥ ሒደትን ለሌሎች ለማስተዋወቅ ምን እየሠራችሁ ነው?
ወ/ሮ እናነይ፡– የአውራ አምባ ማኅበረሰብ መልካም እሴቶችና ታሪክ ለማስተዋወቅና ተሞክሮአችንን ለሌሎች ለማጋራት በርካታ ሥራዎችን እያከናወንን ነው፡፡ የመጀመሪያው ለ50 ዓመታት በፍቅር የዘለቀ ማኅበረሰብ ሒደትና አመሠራረት የሚያትት መጽሐፍ ተዘጋጅቷል፡፡ መጽሐፉን ጥበቡ በለጠና ዘካሪያስ ዐምደብርሃን (ዶ/ር) ‹‹ዝክረ አውራ አምባ ዙምራ›› በሚል ርዕስ አዘጋጅተውታል፡፡ የአውራ አምባን መሥራች ዙምራንና ማኅበረሰቡን በጥልቀት የሚያትት መጽሐፍ ነው፡፡ በሌላ በኩል አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ስለአውራ አምባ ማኅበረሰብ ታሪክና እሴቶችን ለሌሎች የማኅበረሰብ ክፍሎች በሚጠቅም መንገድ ዶክመንተሪ አዘጋጅተዋል፡፡ መጽሐፉ በተለያዩ የመጽሐፍ መደብሮች የሚገኝ ሲሆን ዋጋው 400 ብር ነው፡፡ ማኅበረሰቡ ከተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተወጣጡና ሐሳብ (የሰላም፣ የመተሳሰብ የፍቅርና የእኩልነት) ያሳሰባቸው ናቸው፡፡ ማኅበረሰቡ ለረዥም ዓመታት በሰላምና በእኩልነትና በፍቅር የኖረ ነው፡፡
ሪፖርተር፡- ለኢትዮጵያ ችግሮች የአውራ አምባ ማኅበረሰብ እሴቶች መፍትሔ በዚህ ጉዳይ ምን ትላላችሁ?
ወ/ሮ እናነይ፡– የአውራ አምባ ማኅበረሰብ በሴቶች እኩልነት፣ በልጆችና ሕፃናት መብት በሌሎችም ጉዳይ በርካታ ሥራ ሠርቷል፡፡ ሕፃናት ከልጅነታቸው ጀምሮ የጓደኞቻቸውን መብት እያከበሩና የራሳቸውን መብት እያወቁ በማደጋቸው ለችግሮቹ አይጋለጡም፡፡ ሁሉም ተሳስቦና በማኅበረሰቡ እሴት አምኖበትና እየኖረው በመሆኑ በሰላም ረዥም ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ማኅበረሰቡ የሰው ልጅ ክቡር መሆኑን ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ አቅመ ደካሞችን በመርዳት ይታወቃል፡፡ የማኅበረሰቡን እሴቶች በትክክል ሁሉም ቢተረጉመው አሁን ያሉት ችግሮችን በቀላሉ መቅረፍ ይቻላል፡፡