በአፋን ኦሮሞ ሙዚቃ ስመጥር በሆነው ድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ስም የተዘጋጀው የሙዚቃ ሽልማት ሰኔ 22 ቀን 2014 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ኢሊሊ ሆቴል ተካሂዷል፡፡
በሃጫሉ ሁንዴሳ ፋውንዴሽን አማካይነት የተዘጋጀው ሽልማቱ የተሰጠው በአሥር የሙዚቃ ዘርፎች ሲሆን፣ ሃጫሉ ካረፈበት ዕለት ወዲህ እስከ ዘንድሮ መጋቢት 22 ቀን ድረስ የወጡ የአፋን ኦሮሞ ሙዚቃዊ ሥራዎች ለውድድሩ ቀርበዋል፡፡
የመጀመርያው አሸናፊዎች የሆኑት በምርጥ የሙዚቃ ግጥም ሲሳይ አሰፋ፣ በምርጥ የሙዚቃ ዜማ እንዲሁም በምርጥ ዘፈን፣ በምርጥ የሙዚቃ ቪዲዮ ዮሰን ጌታሁን፣ በምርጥ የሙዚቃ አቀናባሪ ዳዊት ታደሰ፣ በምርጥ ሲኒማቶግራፈር ሽመልስ ታደሰ፣ በምርጥ ዳይሬክተር እንዲሁም በምርጥ ኤዲተር አመንሲሳ ኢፋ፣ በምርጥ አዲስ ወንድ ዘፋኝ ማቲያስ ዘመዴ፣ በምርጥ አዲስ ሴት ዘፋኝ ኮኬት አሰፋ ናቸው፡፡ ለአሸናፊዎች የዋንጫና የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
ፋውንዴሽኑ በመጀመሪያው የሃጫሉ ሁንዴሳ ሽልማት ላይ በኦሮሞ ኪነ ጥበብ ውስጥ ታላቅ አስተዋጽዖ ላበረከቱ ሦስት አንጋፋ አርቲስቶች ማለትም ዘሪሁን ወዳጆ፣ ሀሎ ዳዌና ኢብራሂም አህመድ ዕውቅናና የገንዘብ ሽልማት ሲሰጥ፣ ለአንጋፋው ኮከብ ድምፃዊ አሊ ቢራ የሕይወት ዘመን ተሸላሚ አድርጎታል።