በኢትዮጵያ የእናቶችን የተመጣጠነ ምግብ ዕጥረት፣ የሕፃናት መቀጨጭና መቀንጨርን ችግር ለመፍታት የሚያስችል የ30 ሚሊዮን ዶላር ፕሮግራም መጀመሩን ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ የመቀንጨር ችግር በ1992 ዓ.ም. ከነበረበት 58 በመቶ በ2012 ዓ.ም. ወደ 37 በመቶ የቀነሰ ቢሆንም፣ ከሁለት ዓመት በፊት በቀረበ የመካከለኛ ጊዜ የሥነ ሕዝብና የጤና ዳሰሳ ጥናት፣ አሁንም ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ 5.8 ሚሊዮን ሕፃናት የመቀንጨር ችግር እንዳለባቸው አሳይቷል፡፡
ከ1.2 ሚሊዮን የሚበልጡ ሕፃናት ደግሞ አጣዳፊ የምግብ ዕጥረት እንዳለባቸው ጥናቱ ያሳያል፡፡ ይህ ከሌሎች በማደግ ላይ ካሉ አገሮች ጋር ሲነፃፀር የችግሩ መጠን የከፋ መሆኑን ያሳያል።
መንግሥት የችግሩን ስፋትና ጥልቀት በመገንዘብና የአገሪቱን የምግብና ሥርዓተ ምግብ ዋስትና ተግዳሮቶች ለመፍታት ባለድርሻ አካላትንና አጋር ድርጅቶችን በማቀናጀት የምግብና ሥርዓተ ምግብ ፖሊሲ ስትራቴጂን በ2010 ዓ.ም. አፅድቆ ተግባራዊ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
የጤና ሚኒስቴር የፕሮግራሙን መጀመር አስመልክቶ ባዘጋጀው ዓውደ ጥናት የተገኙት የጤና ሚኒስቴር የእናቶችና ሕፃናት ጤና ዳይሬክተር መሠረት ዘላለም (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ፕሮግራሙ በመላው አገሪቱ በተመረጡ ወረዳዎች በቀጣዮቹ አሥር ዓመታት የሚተገበር ይሆናል።
ስትራቴጂው የነፍሰ ጡርና አጥቢ እናቶችን አመጋገብ በማሻሻል ጤናማነታቸውን ያረጋገጠና የተሻለ እርግዝናና ወሊድ እንዲኖራቸው ለማድረግ እንዲሁም ሕፃናትን ሥር ከሰደደ የምግብ አለመመጣጠንና አጣዳፊ የምግብ ዕጥረት ችግሮች በመከላከል አገራዊ የኢኮኖሚ ዕድገትና ብልፅግናን ለማስተካከል የሚችል ዜጋ ለማፍራት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል።
የፕሮግራም ትግበራው በፓወር ኒውትሪሽን፣ ኤሊኖር ክሮክ ፋውንዴሽን፣ ዘ ኢንድ ፈንድና ሮታሪ ኢንተርናሽናል በተባሉ ለጋሽ ድርጅቶች የገንዘብ ድጋፍ የሚደረግለት ሲሆን፣ በጤና ሚኒስቴር፣ በዩኒሴፍና አክሽን አጌነስት ሀንገር መካከል በተደረገ የጋራ የትግበራ ትብብር ስምምነት ተፈጻሚ እንደሚሆን ጤና ሚኒስቴር በማኅበራዊ ገጹ አስፍሯል፡፡