ሐምሌ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ከወጣው ከ14ኛ ዙር የ20/80 እንዲሁም ከ40/60 ሦስተኛ ዙር ዕጣ አወጣጥ ጋር በተያያዘ የነዋሪነት መታወቂያ አገልግሎት እንዲቆም መደረጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ፡፡
ይህ የከተማ አስተዳደሩ ውሳኔ ዕጣው ከወጣ በሦስት ቀን በኋላ ሐምሌ 4 ቀን 2014 ዓ.ም. በከተማ ሥራ አስኪያጅ በኩል በክፍላተ ከተማና ወረዳዎች ላሉ ወሳኝ ኩነት ምዝገባ ቢሮዎች የተላለፈ ነው፡፡ በዚህም አዲስ መታወቂያ ማውጣትና ማደስን ጨምሮ ከመታወቂያ ጋር የተያያዙ አግልግሎቶች ቆመዋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዲ ፀጋዬ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አገልግሎቱ የቆመው ከጋራ መኖሪያ ቤት ዕጣ አወጣጡ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ወንጀል የመመርመርና ተመዝገቢዎችን ኦዲት የማድረግ ሥራ እየተከናወነ በመሆኑ ነው፡፡
‹‹የጋራ መኖሪያ ቤቱ ደግሞ በአግባቡ ለቆጠበ የከተማው ነዋሪ እንዲተላለፍ ይፈለጋል›› ያሉት ኃላፊው፣ ቤቶቹን ለተገቢ ነዋሪዎች ለማቅረብ ሲባል ከመታወቂያ ጋር ተያይዞ ሊኖር የሚችል ማጭበርበርን ለመከላከል በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አክለውም ‹‹ኦዲት ተጠናቆ ነገሮች እስኪጣሩ ድረስ ለዚህ ዓላማ ሲባል የተወሰደ የጥንቃቄ ዕርምጃ ነው፤›› ሲሉ አገልግሎቱ የቆመበትን ምክንያት አብራርተዋል፡፡
ኦዲት የማድረግ ሥራው በመጠናቀቅ ላይ መሆኑን ያነሱት አቶ አብዲ፣ የኦዲት ሥራው ሲጠናቀቅ የመታወቂያ አገልግሎቱ እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሐምሌ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ያወጣውን ከ25 ሺሕ በላይ የጋራ ማኖሪያ ቤቶች ዕጣ የሰረዘው የቤት ማስተላለፍ መረጃ ስህተት መሆኑን አስታውቆ ነበር፡፡ እንደ አስተዳደሩ ገለጻ ለዕጣው ብቁ ናቸው የተባሉ 79 ሺሕ ያህል ሰዎች የነበሩ ቢሆንም፣ ዕጣውን ለማውጣት የተዘጋጀው ሲስተም ውስጥ የተካተቱት ግን 173 ሺሕ ሰዎች ናቸው፡፡
አስተዳደሩ ዕጣ አወጣጡ ጋር በተያያዘ ኃላፊዎችንና ባለሙያዎችን በቁጥጥር ስር ያዋለ ሲሆን ባለፈው ሳምንት በተካሄደው የከተማዋ ምክር ቤት ጉባዔ ላይ የምክር ቤቱ አባል የሆኑት ሙሉቀን ሀብቱ (ዶ/ር) ያለመከሰስ መብታቸው ተነስቶ በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡
በአጠቃላይ ከዕጣ አወጣጡ ጋር በተያያዘ ወንጀል እስካሁን ድረስ 16 ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል፡፡
የተሰረዘው ዕጣን በድጋሚ በአጠረ ጊዜ ውስጥ እንደሚያወጣ ያስታወቀው አስተዳደሩ፣ አሁን ዕጣ የወጣበትን ሲስተም በድጋሚ በቀጣዩ ዕጣ ላይ እንደማይቀመጥ ገልጿል፡፡ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ማረጋገጫ እንዲሰጡበት እንደሚደረግበት ተነግሯል፡፡