በኢትዮጵያ ከ1941 ዓ.ም. ጀምሮ በሰባ ዓመታት ውስጥ የተፈጸሙ ዋና ዋና የወንጀል፣ የትራፊክና ድንገተኛ አደጋዎች እንዲሁም አስገራሚ መረጃዎችን አሰባስቦ የያዘ መጽሐፍ ለንባብ ቀርቧል፡፡ በአቶ ሙሉጌታ ደንበል ቦሪ የተዘጋጀው መጽሐፍ ርዕሱ፣ ‹‹ወንጀል-ነክና አስገራሚ መረጃዎች›› ይባላል፡፡ ጸሐፊው መጽሐፉን ለማዘጋጀት ካነሳሷቸውና በመቅድማቸው ከገለጿቸው ዓበይት ዓላማዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙባቸዋል፡፡
ልጆችን ያለ አሳዳጊና ቤተሰብን ያለጧሪ በማስቀረት በተፈጸሙ ዘግናኝ የነፍስ ግድያ ወንጀሎች ኅብረተሰቡ በመፀፀት ትምህርት ወስዶና የወንጀልን አስከፊነት በመረዳት በቀጣይ መሰል ወንጀሎችን እንዳይፈጸም ለማስተማር፤ አባይ ጠንቋዮች በዘመናት በኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ላይ ያደረሱትን ግፍና ጭካኔ የተሞላበት ነውረኛ ወንጀሎችን ለማጋለጥና ኅብረተሰቡ ከእነዚህ እኩይ ጠንቋዮች ራሱን እንዲያርቅና እንዲጠብቅ ለማስተማር፣ ለምርምርና ሥርፀት እንዲሁም ለማጣቀሻ መረጃነትና በጽሑፍ ቅርስነት እንዲያገለግል ለማድረግ ነው፡፡
መጽሐፉ በውስጡ ከ1941 እስከ 2011 ዓ.ም. ድረስ በፖሊስና ርምጃው፣ በኢትዮጵያ ድምፅ፣ በሰንደቅ ዓላማችን፣ በአዲስ ዘመንና በአዲስ ልሳን ጋዜጦች ላይ ታትመው የተሠራጩና ለወደፊት ማኅበረሰባችን የወንጀልን አስከፊነት በመረዳት፣ ከወንጀል እንዲርቅና ወንጀልን እንዲፀየፍ በትምህርት ሰጪነታቸው የተመረጡ ዋና ዋና ያልተቆራረጡና ያልተቀነጫጨቡ 545 የወንጀል-ነክ፣ የትራፊክና ድንገተኛ አደጋዎች እንዲሁም አስገራሚ መረጃዎችን ይዟል፡፡
በተጨማሪም ከፌዴራል ፖሊስ፣ ከአዲስ አባባና ከደቡብ ፖሊስ በሳምንታዊ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች የተላለፉ ዋና ዋና ወንጀል-ነክ ዜናዎችን ማሰባሰቡን ጸሐፊው ገልጸዋል፡፡