በአፍሪካ የውስጥ ሊጎች የሚጫወቱ ተጨዋቾች ብቻ ለሚሳተፉበት ቻን የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመርያ ማጣሪያውን ከሱዳን አቻው ጋር ያደረገው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን፣ ተጋጣሚውን በሰፊ ውጤት አሸንፎ ለመጨረሻው ማጣሪያ ማለፉን አረጋግጧል፡፡
በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ውሳኔ በሜዳው እንዳይጫወት ገደብ የተጣለበት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን፣ በምሥራቅ አፍሪካዊቷ ታንዛኒያ ሜዳ ላይ የደቡብ ሱዳን አቻውን ማሸነፍ የቻለው 5 ለ0 በሆነ ድምር ውጤት ነው፡፡
ካፍ ኢትዮጵያና ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ በርካታ የአፍሪካ አገሮች ስታዲየሞች ከስታዲየም ጥራት (ስታንዳርድ) ጋር በተያያዘ አኅጉራዊም ሆነ ዓለም አቀፋዊ ውድድሮችን በሜዳቸው እንዳያስተናግዱ ዕግድ መጣሉ አይዘነጋም፡፡ ይህን ውሳኔ ተከትሎ ነው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን እስካሁን አራት ጨዋታዎችን ከሜዳው ውጭ እንዲጫወት ተገዶ የቆየው፡፡
ምዕራብ አፍሪካቷ ኮትዲቯዋር በሚቀጥለው ዓመት ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ግብፅ፣ ማላዊና ጊኒ ምድብ የተደለደለችው ኢትዮጵያ፣ በምድብ ማጣሪያው ከማላዊና ከግብፅ ጋር ተጫውታለች፡፡ ከሰሞኑ ደግሞ ለቻን ማጣሪያ ደቡብ ሱዳንን በታንዛኒያ ስታድየም የደርሶ መልስ ጨዋታ ማድረጓ ልብ ይሏል፡፡
በቀጣይም ካፍ በአገሪቱ ስታድየሞች ላይ ያስቀመጠው ዝቅተኛ መሥፈርት በመሻሻያ ግንባታ ችግሩ እስካልተቀረፈ ድረስ፣ ብሔራዊ ቡድኑ የሚያደርጋቸው ጨዋታዎች በስደት እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ የደቡብ ሱዳን አቻውን በሰፊ ውጤት ያሸነፈው ብሔራዊ ቡድኑ፣ ቀጣይ ተጋጣሚው የሩዋንዳ አቻው ጋር ሲሆን፣ የሁለቱ አሸናፊ ማለትም የኢትዮጵያና የሩዋንዳ አሸናፊ ለቀጣዩ ቻን የአፍሪካ ዋንጫ ትኬት ከሚቆርጡ አገሮች አንዱ ይሆናል፡፡