በፊላንድ ሔልንስኪ አንድ ብሎ ሦስት አሠርታትን መሻገሩ የሚነገርለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና፣ ባለፈው ሳምንት 18ኛውን የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአሜሪካ ዩጅን ከተማ በኦሪገን ዩኒቨርስቲ ስታዲየም አከናውኗል፡፡ በሔልንስኪው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በማራቶን አንድ የብር ሜዳልያ በማስመዝገብ ተሳትፎዋን አንድ ብላ የጀመረችው ኢትዮጵያም፣ ዘንድሮ አራት የወርቅ፣ አራት የብርና ሁለት የነሐስ በድምሩ 10 ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ከአስተናጋጇ አሜሪካ ቀጥላ የተቀመጠችበትን ውጤት አስመዝግባለች፡፡
ባለፈው ሐሙስ ሐምሌ 21 ቀን 2014 ዓ.ም. ድል ላስመዘገበው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን፣ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በተገኙበት በብሔራዊ ቤተ መንግሥት የአቀባበልና የምሥጋና ፕሮግራም ተከናውኗል፡፡ በሻምፒዮናው የተመዘገበው ውጤት በትብብር ከተሠራ ኢትዮጵያውያን በሁሉም መስክ አሸናፊ የሚሆኑበት ጊዜ ሩቅ እንደማይሆን በመድረኩ ተነግሯል፡፡
በቤተ መንግሥቱ አቀባበልና ምሥጋና ፕሮግራም ላይ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ ስለኢትዮጵያውያን አትሌቶች ገድል ብዙ መነገሩን ገልጸው፣ በተለይም በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በውስጥም፣ በውጪም በብዙ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ውስጥ በምትገኝበት ወቅት በመሆኑ ድሉ ከድልም በላይ ትልቅ ድል እንደሆነ ነው የተናገሩት፡፡
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮች የአሸናፊነት ሜዳልያዎችን በተደጋጋሚ አስመዝግበዋል ያሉት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ፣ ‹‹ይህ የዘንድሮ ድል ግን ከሜዳልያም ያለፈ ነው፡፡ ይህ ድል የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ከሌሎች አገሮች ሰንደቅ ዓላማ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ ከማድረግ ያለፈ ነው፡፡ የአገራችንና የሕዝባችን መዝሙር መዘመሩ ብቻ ሳይሆን፣ በዓለም አደባባይ ትልቅ ክብረ ወሰን ያጎናፀፈን ነው፤›› ብለዋል፡፡
ውጤቱ ‹‹ለተጨነቀው፣ ላዘነው፣ ለተከፋው፣ ኑሮ ለከበደው፣ እንደ አገር ‹የት ነን?› ለሚለው ሁሉ ፈገግታን ያስገኘ፣ የፈለገው ቢባል ለመከፋፈል ቢሞከርም፣ እንደ ሕዝብ ችግር እንደሌለ፣ ላንግባባ እንችላለን ግን እንደማንጠላላ አትሌቶቻችን አሳይተዋል፤›› ካሉ በኋላ፣ በአጠቃላይ ድሉ በድቅድቅ ጨለማ ብርሃን እንዳለ አመላካች ስለመሆኑ ጭምር ተናግረዋል፡፡
የፕሬዚዳንቷ ንግግራቸውን ቀጥለው፣ ‹‹ዛሬ እናንተ የሳያችሁን የአሸናፊዋን ኢትዮጵያ ገጽታ ነው፡፡ ይሁንና አጥፊውም፣ ጨካኙም ያለበት አገር ነው፡፡ የአረመኔነት ጫፍ ያየንበት አገር ነው፤›› ብለው የሚበድለው፣ የሚያጭበረብረው፣ የሚቦረቡረው፣ በዚህም የተነሳ ዜጎች የሚገደሉባት፣ በርካታ ከቤተሰብ ጋር መገናኘት ያልቻሉ፣ በናፍቆትና በጭንቀት የሚገኙ በትልቁ ማንነት ለሞት ሲያደርስ የታየበት ከመሆኑ ባሻገር፣ በእሱ ሳይሆን በሌሎች መበልፀግ ጎልቶ የሚታይበት እውነታ ላይ መሆኗን ተናግረዋል፡፡ ቀኑም አትሌቶቹ ያስመዘገቡትን ድል የምናከብርበት ሳይሆን፣ ትልቅ ትምህርት የምንወስድበት ስለመሆኑ ጭምር ነው ፕሬዚዳንቷ ያመላከቱት፡፡
በቤተ መንግሥት በተዘጋጀው ፕሮግራም፣ በውድድሩ ለተካፈሉ አትሌቶችና አሠልጣኞች እንዳስመዘገቡት ውጤት ከ50 ሺሕ ብር እስከ 2.5 ሚሊዮን ብር የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
በርካቶች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በኦሪገን የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ያስመዘገቡት ድል ቢያስደስታቸውም ቅሉ፣ ኢትዮጵያ በተለይም በአሁኑ ወቅት የምትገኝበትን ሁኔታ በመጥቀስ በተደበላለቀ ስሜት ሆነው ነው አስተያየታቸውን ሲሰጡ የተደመጡት፡፡
የብዙዎቹ አስተያየት አንድነት፣ ኃይልና የአሸናፊነት ሚስጥር መሆኑ፣ ከዚህ አኳያ ልክ እንደ አትሌቲክሱ ሁሉ በሁሉም መስክ በመተባበር ኢትዮጵያን አሸናፊ ማድረግ ይገባል፡፡
የድሉ ባለቤት የሆኑ አትሌቶችም ይህንኑ አስተያየት በመጋራት ከተናገሩት መካከል፣ በማራቶን የብር ሜዳልያ ያስመዘገበው ሙስነት ገረመው፣ ‹‹አንድ ስንሆን ሁሌም አሸናፊ እንሆናለን፤›› ብሏል፡፡ ሌሎችም በተመሳሳይ የአሸናፊነታቸውን ሚስጥር ከመናገር ይልቅ፣ አገሪቱ የምትገኝበትን ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ትኩረቱን ያደረገ ነበር፡፡
ቡድኑ ከቤተ መንግሥቱ መርሐ ግብር ቀጥሎ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዕውቅናና የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ተደርጎለታል፡፡ በዕውቅና ፕሮግራሙ ላይ የተገኙት ከንቲባ አዳነች አበቤ አትሌቶቹን እንደ አልማዝ ደምቀው ኢትዮጵያውያንን ያደመቁ ‹‹የቁርጥ ቀን ልጆች፤›› ሲሉ አወድሰዋቸዋል፡፡
ከንቲባዋ፣ ‹‹ኢትዮጵያ የልጆቿ ብቻ ናት፣ ልጆቿ ደግሞ አንድ ልታደርጓት በኦሪገኑ 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ፊት ቆማችሁ፤›› ብለው፣ ‹‹ኢትዮጵያ ማለት እናንተ፣ በእናንተ ውስጥ ያለው ወኔ ነው፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ድል ማድረግ ሥሪታችሁ ነው፣ ልክ እንደ አባቶቻችን በማሸነፍ ውስጥ አገር በማስከበር የክብር ጌጥ ናችሁ፤›› በማለት፣ ለኢትዮጵያውያን አትሌቶች ያላቸውን አድናቆት የገለጹት ከንቲባ አዳነች፣ ‹‹ታሪክን ለትውልድ ማውረስ፤›› ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያ የነፃነትና የመቻቻል መዝገብ ስለመሆኗ ጭምር ነው የተናገሩት፡፡
‹‹ኢትዮጵያ በልጆቿ ብርቱ ተጋድሎ ከብተና የዳነች ናት፤›› ያሉት ከንቲባ አዳነች ድሉን አስታከው ሲናገሩ፣ ‹‹ኢትዮጵያውያን ፈተና የማይፈታን ይልቁንም የሚያፀናን፣ መሰናክል የማያቆመን ይልቁንም የሚያስተምረን፣ ወራሪዎችና ሴረኞች የማይበትኑን ይልቁንም የሚያጠነክሩን፤›› በማለት አትሌቶቹ ያስመዘገቡት ውጤት ለዚህ አንዱና ትልቁ ማሳያ እንደሆነ ነው የገለጹት፡፡
በዕውቅና ፕሮግራሙ ልዩ ተሸላሚ የሆነችው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር ደራርቱ ቱሉ በበኩሏ፣ ለልዑካን ቡድኑ ለተደረገው ዕውቅና ምሥጋናዋን አቅርባለች፡፡ ‹‹የእኔ አስተሳሰብን በእኛ›› በመቀየር አገርን ማስቀደም እንደሚያስፈልግም አትሌት ደራርቱ ቱሉ ተናግራለች፡፡
በኢትዮጵያ ካለው በተለይም በማዕከላዊ መንግሥትና በትግራይ ክልላዊ መንግሥት መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ዕልባት እንዲያገኝም ጠይቃለች፡፡ በችግሩ ምክንያት ከቤተሰቦቻቸው የተለያዩ አትሌቶች ቤተሰቦቻቸውን እንዲያገኙ፣ እንዲሁም በትግራይ የሚገኙ አትሌቶችም ወደ ቀድሞ ሥራቸው እንዲመለሱና ማዕከላዊ መንግሥትና የትግራይ ክልል ባለሥልጣናት ሰላም እንዲያወርዱ ጠይቃለች፡፡
የባህልና ስፖርት ሚኒስትሩ ቀጀላ መርዳሳ በበኩላቸው፣ ‹‹ድሉ ከፋፋይ አስተሳሰቦችን ተሻግሮ አንድነትን በተግባር የሰበከ ነው፤›› በማለት ነበር ለአትሌቶቹ ያላቸውን ክብር የገለጹት፡፡
በመጨረሻም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለኦሪገኑ የልዑካ ቡድን በጥቅል 10 ሚሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብ አበርክቷል፡፡ በተጨማሪ በውድድሩ የነሐስ ሜዳልያ ላስመዘገቡ አትሌቶች 250 ካሬ ሜትር፣ የብር ሜዳልያ ላስመዘገቡ አትሌቶች 350 ካሬ ሜትር፣ እንዲሁም የወርቅ ሜዳልያ ላስመዘገቡ ደግሞ 500 ካሬ ሜትር የመሬት ስጦታም አበርክቷል፡፡