የሔፒታይተስ ቫይረስ የጉበት ብግነት ወይም መቆጣት የሚያስከትል ሲሆን፣ የሚከሰተውም በተለያዩ በዓይን በማይታዩ ተዋህስያን፣ በአልኮል መጠጥ፣ በአንዳንድ መድኃኒቶችና መርዛማ በሆኑ ኬሚካሎች አማካይነት ነው፡፡ በዓለም ላይ የተለያዩ በቫይረሱ አማካይነት የሚመጡ የሔፒታይተስ ዓይነቶች ሲኖሩ እነዚህም ኤ፣ ቢ፣ ሲ፣ ዲ እና ኢ በመባል ይታወቃሉ፡፡
ከእነዚህም ውስጥ በብዛት በዓለም ላይ ተሠራጭተው በሰው ጤና ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱ የሚገኙት ሔፒታይተስ ቢ እና ሲ በመባል የሚታወቁት የቫይረስ ዓይነቶች ናቸው፡፡ ሔፒታይተስ በሽታ የጉበት ሴሎችን በመጉዳትና በማጨማተር እንዲሁም ጉበት ካንሰርን በማስከተል ዕድሜ ዘለቅ ጉዳት ያስከትላል፡፡
የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ደረጀ ድጉማ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በዓለም ጤና ድርጅት መረጃ መሠረት በዓለም ላይ ወደ 325 ሚሊዮን የሚሆነው ሕዝብ በሔፒታይተስ ቫይረስ ምክንያት ለዕድሜ ዘለቅ የጉበት ኢንፌክሽን ተጠቂ ሲሆን፣ ከዚህም ውስጥ በየዓመቱ 1.1 ሚሊዮን የሚገመት ሕዝብ ለሞት ይዳርጋል፡፡ በየ30 ሰከንዱ አንድ ሰው በቫይረሱ አማካይነት በሚመጣ የጉበት በሽታ ሕይወቱን ያጣል ተብሎም ይገመታል፡፡
ከኤችአይቪ ጋር ሲነፃፀርም በኤችአይቪ ከሚያዘው ሰው ይልቅ በሔፒታይተስ የሚያዘው ሰው ቁጥር በዘጠኝ እጥፍ ይበልጣል፡፡
ሔፒታይተስ ቢ በብዛት በሚከሰትባቸው በተወሰኑ የዓለም ክፍሎች ያሉ ሰዎች ማለትም እንደ እስያና የአፍሪካ የተወሰኑ ክፍሎች፣ ከሰሃራ በታች ባሉ አገሮች፣ ደቡብ አሜሪካ፣ ምዕራብ አውሮፓና መካከለኛው ምሥራቅ በበሽታው የመያዝ ዕድላቸው በእጅጉ ከፍ ያለ ነው፡፡ በርካታ ሰዎች በበሽታው ስለመያዛቸው እንኳን አያውቁም፣ እንዲሁም የበሽታው ምልክቶችም አይታይባቸውም፡፡
በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2017 በተሠራ የዳሰሳ ጥናት፣ በሽታው በስፋት ተሠራጭቶ ከሚገኝባቸው አገሮች መካከል መሆኗንና እስከ 9.4 በመቶ በሔፒታይተስ ቢ እና 3.1 በመቶ በሔፒታይተስ ሲ ቫይረስ ተጠቂ እንደሚገኝ ማሳየቱን ገልጸዋል፡፡
በሔፒታይተስ ቢ እና ሲ ቫይረስ በተበከለ ደም፣ ንፅህናቸው ባልተጠበቁ ስለታም መሣሪያዎች፣ በጎጂና ልማዳዊ ድርጊቶች፣ በግብረ ሥጋ ግንኙነት እንዲሁም በወሊድ ጊዜ ከእናት ወደ ልጅ ሊተላለፍ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
በርካታ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ስለመያዛቸው አለማወቃቸውን ተከትሎ፣ ‹‹ዝምተኛው በካይ›› የተባለው በሽታ፣ ቫይረሱን በደማቸውና በሌሎች በተበከሉ የሰውነታቸው ፈሳሾች ወደ ሌሎች እንደሚያዛምቱ፣ ለብዙ ዓመታት ድምፁን አጥፍቶ እንደሚቆይ፣ በጊዜ ሒደት በጉበት ላይ ጉዳት እንደሚያደርስ፣ በፀና የታመሙት ጉበታቸው ሥራ የማቆምና በስተመጨረሻም ለጉበት ካንሰር እንደሚያጋልጣቸው አመልክተዋል፡፡
‹‹የጉበት በሽታ ሕክምናና እንክብካቤ ተደራሽነትን ለሁሉም›› በሚል መሪ ቃል ሐምሌ 21 ቀን 2014 ዓ.ም. ታስቦ የዋለውን የዓለም የሔፒታይተስ ቀን አስመልክተው ሚኒስትር ዴኤታው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳብራሩት፣ ለሔፒታይተስ ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑ የማኅበረሰብ ክፍሎች ሔፒታይተስ ቢ እና ሲ ካለበት ሰው ጋር የትዳር፣ የወሲብ አጋር የሆኑ ወይም በቅርበት የሚኖሩ አዋቂዎችና ሕፃናት፣ የቫይረሱ ሥርጭት በብዛት ባለባቸው አካባቢዎች መውለድ/መኖር፣ ከተለያዩ ሰዎች ጋር ወሲብ የሚፈጸሙና ጥንቃቄ የጎደለው የወሲብ ግንኙነት የሚያደርጉ ናቸው፡፡
በሔፒታይተስ ከተያዘች እናት የተወለደ ሕፃን፣ የጤና ባለሙያዎችና ሌሎች ሠራተኞች ከሥራቸው ጋር በተያያዘ በሚገጥማቸው የደም ንኪኪ፣ አደገኛ ዕፅ ተጠቃሚዎች በሚወጉት መርፌ፣ ንፅህና ባልጠበቁ መሣሪያዎች የሚነቀሱና ሰውነታቸውን የሚበሱ ሰዎችና የኩላሊት እጥበት የሚደረግላቸው ታካሚዎች ተጋላጭ ከሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች እንደሆኑም ገልጸዋል፡፡
በሽታውን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ልዩልዩ ጥንቃቄዎች መወሰድ እንዳለባቸው ገልጸው፣ ከጥንቃቄዎቹና ዕርምጃቹ መካከል በቀጥታ ደምንም ሆነ የሰውነት ፈሻስን ከመንካት መቆጠብ፣ ደምና የደም ውጤቶች ልገሳ በአግባቡ መመርመር፣ ጥንቃቄ ከጎደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነት ራስን መጠበቅና ኮንዶም በአግባቡ መጠቀም፣ ሕገወጥ የሆኑ መድኃኒቶችንና የተሳሳተ የመድኃኒት ትዕዛዝን አለመጠቀምና አለመወጋት፣ ስለታም የሆኑ ነገሮችን፣ ምላጭ፣ የጥርስ ቡሩሽ፣ የጆሮ ኩክ ማፅጃና የጥፍር መቁረጫ በጋራ አለመጠቀም እንደሚገኙበት ጠቁመዋል፡፡
ጥርስ ሕክምና፣ ለደረቅ መርፌ ሕክምና፣ ለንቅሳት እንዲሁም ጆሮንና ሌላውን የሰውነት ክፍል ለመብሳት መርፌዎችንና ሌሎች መገልገያዎችን በጋራ አለመጠቀም፣ የፈሰሰ ደምን ለማፅዳት የመከላከያ አልባሳትና ጓንት መጠቀም፣ የደም ንኪኪ ካጋጠመ ወይም ከተፀዳ በኋላ እጅን በውኃና በሳሙና በሚገባ መታጠብ፣ የሔፒታይተስ ‹‹ቢ››ን ክትባት ለሕፃናትና ለተጋላጭ የማኅበረሰብ ክፍሎች እንዲወስዱ ማድረግ መወሰድ ከሚገባቸው ጥንቃቄዎችና ዕርምጃዎች ተጠቃሽ መሆናቸውንም አክለዋል፡፡
እንደ ሚኒስትር ዴኤታው፣ በኢትዮጵያ የሔፒታይተስ ቫይረስን ለመቆጣጠርና ለመከላከል የሚያስችሉ በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ ሲሆን፣ ከእነዚህም አንዱ የግንዛቤ ማስጨበጫ ነው፡፡
ለዚህም ዕውን መሆን በአገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የሔፒታይተስ ፕሮግራም ለማጠናከርና የሕክምናውን ተደራሽነት ለማስፋፋት በሚረዳ መልኩ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ተዘጋጅቶና ታትሞ ተሠራጭቷል፡፡ እንዲሁም አዳዲስ የዓለም ጤና ድርጅት ምክረ ሐሳብን ባካተተ መልኩ የሕክምናና ክብካቤ መመርያ ተከልሶ በኅትመት ላይ ይገኛል፡፡
በቫይረስ አማካይነት ስለሚከሰት የጉበት ሕመምና ካንሰር ግንዛቤ ለማሳደግ ለጤና ባለሙያዎች የሚሆኑ የሥራ አጋዥ መልዕክቶችና የታካሚዎች ማስተማሪዎች መዘጋጀታቸውን እንዲሁም ለማኅበረሰብና ታማሚዎች ማስተማሪያ የሚሆን መልዕክቶችም መሠራጨታቸውን ገልጸዋል፡፡
የጤና ሚኒስቴር የሔፒታይተስ ቢ እና ሲ ምርመራና ሕክምናን ለማስፋፋትና ተደራሽ ለማድረግ የምርመራና የሕክምና መመርያ በማውጣት ወደ ሥራ የገባ ሲሆን፣ በአዲስ አበባ ከተማና በክልሎች በተመረጡ የጤና ተቋማት አገልግሎቱን ለማጠናከርና ለማስፋፋት ከክልል ጤና ቢሮዎች ጋር በቅርበት በመሥራት ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡
‹‹የቫይራል ሔፒታይተስ ምርመራና ሕክምና የሚሰጡ ተቋማትን በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የማስፋት ሥራ መሠራቱን፣ ከዚህ በፊት አገልግሎቱን ይሰጡ ከነበሩ 13 ጤና ተቋማት ወደ 90 ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል፡፡
የሔፒታይተስ ቢ ኢንፌክሽንን በክትባት መከላከል ስለሚቻል፣ የሔፒታይተስ ቢ ክትባትን ከመሠረታዊ የክትባት መርሐ ግብር ጋር በማቀናጀት ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ለሕፃናት እየተሰጠ ሲሆን፣ ሕፃናት እንደተወለዱ በ24 ሰዓት ውስጥ የሚሰጠውን የሔፒታይተስ ክትባት በአገር ውስጥ ለማምረት የሙከራ ትግበራው ተጠናቆ ወደ አገር አቀፍ ደረጃ ለማስፋት በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡