Thursday, September 21, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊከኦቲዝም ጋር የሚኖሩትን ወደ ሥራ የማሠማራት ጅማሮ

ከኦቲዝም ጋር የሚኖሩትን ወደ ሥራ የማሠማራት ጅማሮ

ቀን:

አካል ጉዳተኛ ጉዳት አልባ የሆኑ ሰዎች ሊያከናውኗቸው የሚችሉ ልዩ ልዩ ተግባራትን ከማከናወን የሚያዳግተው ነገር የለም፡፡ ለዚህም በዓለም በተለያዩ ሙያዎች ተሰማርተው ከፍተኛ ዝናንና አድናቆትን ያተረፉ አካል ጉዳተኞች መኖራቸው ማሳያ ነው፡፡ በኢትዮጵያም በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ተመድበው ሥራን የሚመሩና የሚያስተባብሩ አካል ጉዳተኞችን ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡

አካል ጉዳተኞች እንደ ጉዳታቸው መጠን እየታየ፣ ችሎታቸውና ብቃታቸው እየተመዘነ በሚመደቡበት ቦታ ሥራ ከመጀመራቸው በፊት ለሚያከናውኑት ሥራ በቅድሚያ ገለጻ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡ ከዚህ አኳያ ኦቲዝምና ተዛማጅ የአዕምሮ ዕድገት እክል ያለባቸው ወጣቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ የሚያስችላቸውን ሥልጠና አግኝተዋል፡፡

ኒያ መልካም ፍላጎትና ራዕይ ፋውንዴሽን ጆይ ኦቲዝም ማዕከል በልዩ ልዩ ሥራዎች ያዘጋጀውን ሥልጠና በመከታተል ያጠናቀቁና ከኦቲዝም ጋር የሚኖሩ ወጣቶችን ለምረቃና ለሥራ አብቅቷል፡፡

በማዕከሉ ለ20 ዓመታት የተከታተሉትን ሥልጠና ያጠናቀቁ ወጣቶችም ሐምሌ 29 ቀን 2014 ዓ.ም. ተመርቀዋል፡፡

የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ እሌኒ ዳዊት እንደገለጹት፣ ተመራቂ ወጣቶቹ በማዕከሉ በቆዩባቸው ዓመታት በምግብና በፅዳት ሥራዎች፣ እክል ያለባቸውን ልጆች በመጠበቅና በመንከባከብ ላይ ያተኮሩ ሥልጠናዎችን ተከታትለዋል፡፡

ከዚህም ሌላ የተግባቦት አቅማቸውን የማሳደግ፣ የሚነገራቸውን በጥሞና በማዳመጥ ተግባራዊ ማድረግ፣ የሥራ መግቢያና መውጫ ሰዓትን ማክበርና ባለጉዳዮችን በክብር ተቀብሎ የማስተናገድ ኃላፊነት መወጣት የሚያስችላቸውን ዕውቀት መቅሰማቸውንም አክለዋል፡፡

ኦቲዝምና ተዛማጅ የአዕምሮ ዕድገት እክል ያለባቸው ተመራቂ ወጣቶቹ ከሚቀጥለው ዓመት የመጀመርያ ወር ጀምሮ የፋውንዴሽኑ ተቀጣሪ ሠራተኞች ሆነው እንደሚያገለግሉ፣ ሥራ ከመጀመራቸው አስቀድሞ ገለጻ እንደሚደረግላቸው የተሞክሮ ልውውጥም እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡

ፋውንዴሽኑ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ኦቲዝምና ተዛማጅ የአዕምሮ ዕድገት እክል ያለባቸውን 300 ሕፃናት ወጣቶች እንዲሁም ቤተሰቦቻቸው ከተጋረጡባቸው ዘርፈ ብዙ  ማኅበራዊ፣ ሥነ ልቦናዊና አካባቢያዊ ጉዳቶች መታደጉን፣ ለሌሎች 80 ልጆችና ቤተሰቦቻቸው ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ የሆኑ ልዩ ልዩ ድጋፎች በማድረግ ላይ መሆኑን፣ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ 68 ወጣቶችን በማዕከሉ ተቀብሎ በመንከባከብ ላይ እንደሚገኝና በሚቀጥለው ዓመት ተጨማሪ 80 ወጣቶችን ተቀብሎ ለመንከባከብ ማቀዱን አስረድተዋል፡፡

ማዕከሉ የሚያከናውነውን ሰብዓዊ አገልግሎት አጠናክሮ ለመቀጠል እንዲያስችለው በአዲስ አበባ ከተማ ሲኤምሲ አካባቢ በ5,000 ሜትር ካሬ ቦታ ላይ የልህቀት፣ የጥናትና የምርምር ማዕከል ከ350 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ እያስገነባ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሯ ጠቁመዋል፡፡

ግንባታው በመፋጠን ላይ የሚኘው ይኼው ሕንፃ ለልዩ ልዩ አገልግሎቶች የሚውሉ በርካታ ክፍሎች እንደሚኖሩት፣ ከእነዚህም መካከል 50 አልጋዎችን የሚይዝ የመኝታና የተሟላ የሕክምና ድጋፍ የሚሰጡባቸው ክፍሎች ተጠቃሾች መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

እንደ ዋና ዳይሬክተሯ፣ ሕንፃውን ለማጠናቅቅ ከዓመታት በፊት የወጣው አጠቃላይ የወጪ ተመን፣ አሁን ባለው ከፍተኛ ግንባታ ዕቃዎች የዋጋ ንረት አንፃር  ሲታይ ከሦስት እጥፍ በላይ ያደገ በመሆኑ ከሁሉም ኢትዮጵያዊ ከፍተኛ ድጋፍ የሚጠይቅ ሆኗል፡፡

የፋውንዴሽኑ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሳራ ሀሰን፣ ‹‹የሰይጣን ሥራ ነው በሚል የተሳሳተ አመለካከት እጆችና እግሮቻቸው በብረት ታስረው ሰው እንዳያያቸው ለብዙ ዓመታት ቤት ውስጥ እንዲቆዩ የተደረጉ ኦቲዝምና ተዛማጅ የአዕምሮ ዕድገት እክል ያደረባቸው በርካታ ወጣቶች ፋውንዴሽኑ ባካሄደው ተከታታይ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ አማካይነት ከእስር ተፈትተውና ከቤት ወጥተው የሥልጠናና የትምህርት ተጠቃሚ ለመሆን በቅተዋል፤›› ብለዋል፡፡

የወጣቶቹም ቤተሰብ፣ ዘመድና አዝማድ ካደረባቸው መሸማቀቅ ተላቅቀው ቀና ብለው መንቀሳቀስ እንዲጀምሩ፣ ችግሩ ያለባቸውንም ልጆቻቸውን ለአገልግሎት ወደ ማዕከሉ ማምጣት መጀመራቸውን የቦርድ ሰብሳቢዋ ገልጸው፣ ሆኖም ግን ማዕከሉ በቂ ቦታና አቅርቦት ባለመኖሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ልጆች ተመዝግበው ወረፋ በመጠባቅ ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ከተመራቂዎችም መካከል ወጣት ዳንኤል ኤፍሬም በሥልጠናው የተግባቦት ክህሎቱን በሚገባ እንዳሻሻለ፣ ራሱን ችሎ እንደሚመገብ በአጠቃላይ ድጋፍ ፈላጊ ከመሆን እንዲላቀቅና በአሁኑ ጊዜ የ11ኛ ክፍል ተማሪ እንደሆነና የኮምፒዩተር ሳይንስ ባለሙያ የመሆን ፍላጎት እንዳደረበት ተናግሯል፡፡

ኒያ መልካም ፍላጎትና ራዕይ ፋውንዴሽን ጆይ ኢቲዝም ማዕከል ኦቲዝምና ተዛማጅ የአዕምሮ ዕድገት እክል ያለባቸውን አራት ልጆች ተቀብሎ የማሠልጠንና የመንከባከብ ሥራ የጀመረው በግንቦት 1994 ዓ.ም. ነበር፡፡ መሥራቿም የኢትዮጵያ የኦቲዝም ጀግኒት የሆኑትና ከአንድ ዓመት በፊት ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ወ/ሮ ዛሚ የኑስ ናቸው፡፡      

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርት ምን ይዟል?

ለአሜሪካ ድምፅ አማርኛ ዝግጅት የስልክ አስተያየት የሰጡ አንድ የደንበጫ...

መንግሥት በአማራ ክልል ለወደሙ የአበባ እርሻዎች ድጋፍ እንዲያደርግ ተጠየቀ

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአማራ ክልል የተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት በቢዝነስ...

አምናና ዘንድሮ!

እነሆ መስከረም ጠብቶ በአዲስ መንፈስ ተሞልተን መንገድ ጀምረናል። ‹‹አዲስ...