Wednesday, October 4, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ኢትዮጵያን የአፍሪካ ጭራ አናድርጋት!

ኢትዮጵያ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በግብርና፣ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በቴክኖሎጂና በመሳሰሉት የልማት መስኮች አንገቷን ቀና የምታደርግባቸው እንቅስቃሴዎች እየታዩ መሆናቸው ያበረታታል፡፡ ሰሞኑን በኢትዮጵያ የነፃ ንግድ ቀጣና ሥርዓት በመዘርጋት ሥራ ለማስጀመር ዝግጅት መደረጉ ትልቅ ግምት ይሰጠዋል፡፡ የነፃ ንግድ ቀጣናው ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ጋር ትስስር ለመፍጠር የሚያስችላት አቅም የሚያስገኝላት ሲሆን፣ በተፈጥሮ የታደለቻቸውን ፀጋዎች በሚገባ በመጠቀም ከአስመራሪው ድህነት ለመገላገልም ይረዳታል፡፡ ከልማቱ ጎን ለጎን ትኩረት የሚያስፈልጋቸው መሠረታዊ ጉዳዮችም መዘንጋት የለባቸውም፡፡ የበጋ ስንዴ አምርታ ሕዝቧን በምግብ ምርት ራሱን ካስቻለች በኋላ ለኤክስፖርት የምትዘጋጅ፣ ከታላቁ የህዳሴ ግድብና ከሌሎች ኃይል ማመንጫዎች የምታገኘውን የኤሌክትሪክ ኃይል ለጎረቤቶቿና ለሌሎችም ለማቃመስ የምታልም፣ ወጣቶቿን በትምህርት አንፃ ለታላቅ ቁምነገር ለማብቃት ስትል የምትማስን፣ በተለያዩ ችግሮች ውስጥ እያለፈ ሁሉን ችሎ የሚኖር ብርቱና ጨዋ ሕዝብ ያላትና በሙሉ አቅም ከተሠራባት በአፍሪካ አስደናቂ መሆን የምትችል አገር ይዞ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መስነፍ ተገቢ አይደለም፡፡

መሰንበቻውን በጎረቤት ኬንያ ምርጫ ሲካሄድ ሰንብቶ ዘግይቶም ቢሆን ውጤቱ ተሰምቷል፡፡ በኬንያ ሚዲያው፣ የሲቪል ማኅበረሰቡ፣ የሠራተኛ ማኅበራት፣ የተለያዩ የሙያና የጥቅም ማኅበራት፣ የሕግ ባለሙያዎች፣ የማኅበረሰብ ተወካዮችና የመሳሰሉት ከቅድመ ምርጫ እስከ ድኅረ ምርጫ የነበራቸው ተሳትፎና እንቅስቃሴ ለሰብዓዊና ለዴሞክራሲያዊ መብቶች የተሰጠውን ቦታ በሚገባ ያመለክታል፡፡ ኬንያውያን በነፃነት የሚፈልጉትን መምረጣቸው ብቻ ሳይሆን፣ ውጤቱን ያዘገየውንና ውዝግብ የፈጠረውን የምርጫ ኮሚሽን በግልጽ በሚዲያ ሲሞግቱ መታዘብ ተችሏል፡፡ ኮሚሽኑ በሚያሳዝን ሁኔታ አንድነቱን አጥቶ ውጤት ሲገልጽም፣ በተለያዩ አደረጃጀቶች ውስጥ የሚገኙ የኬንያ ልሂቃን በሕግ አምላክ እያሉ ነው፡፡ ምንም እንኳ ኬንያ በምርጫ ጊዜ ችግር የማያጣት ብትሆንም፣ በምሥራቅ አፍሪካ የተሻለች አገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ በብዙ ነገሮች ወደኋላ የቀረች መሆኗ የታወቀ ነው፡፡ በምሥራቅ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ አኅጉር ትልቅ ከሚባሉ አገሮች አንዷ መሆን የሚገባት ኢትዮጵያ፣ ለዘመናት ከተፀናወታት የፀረ ዴሞክራሲ ድብርት አላቆ ገጽታዋን ለመለወጥ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ መንግሥትም ሆነ ሌሎች የፖለቲካ ተዋንያን ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡

በኢትዮጵያ ለብዙ ዓመታት የተፈራረቁ ገዥዎች የየራሳቸውን አሻራ ጥለው አልፈዋል፡፡ ሁሉም እንዳከናወኑት በጎና ክፉ ተግባር የሚታወሱበት ይኖራቸዋል፡፡ በዚህ ዘመን ደግሞ እንደ ነገሥታቱ ወይም ከዚያ ቀጥሎ እንደመጡት መሪዎች ግለሰባዊ ተክለ ሰብዕና ላይ ከማተኮር፣ ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲፈጠርና ተቋማዊ አሠራሮች ባህል እንዲሆኑ ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ትናንት በተከናወኑ በጎና አይረቤ ሥራዎች ላይ ከመነታረክና አላስፈላጊ ውዝግቦችን ከመፍጠር፣ የዘመኑ ኢትዮጵያ እንዴት ተመርታ የተሻለች አገር ትሁን የሚለው ላይ ቢሠራ ከትውልድም ከታሪክም ተጠያቂነት ያድናል፡፡ ለአገር የመሪዎች ፋይዳ ትልቅ ቦታ እንደሚኖረው ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ነገር ግን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚገነባው በሁሉም ወገኖች ትብብር ስለሆነና ተቋማትን ማጠናከር ደግሞ የማይታለፍ ተግባር ስለሆነ፣ ሁሌም የቤት ሥራ መሆን ያለበት በርካቶች የአመራር ክህሎት እንዲኖራቸው ማብቃት ነው፡፡ ይህንን ማድረግ ሲቻል የመሪን ትዕዛዝ እየጠበቁ ብቻ መንቀሳቀስ አይቻልም፡፡ ሁሉም በዕቅድ የተሰጠውን ሥራ እያስፈጸመ ውጤቱን ያስለካል፡፡ ብቃቱን በሚገባ ማሳየት የቻለ የመሪነት ልጓሙን የመጨበጥ ዕድሉ ይሰፋል፡፡ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ተደማጭ ያደርጋታል፡፡

በኢትዮጵያ ለብዙ ጊዜ ያስቸገረው የፖለቲካ ምኅዳር መሠረታዊ ለውጥ ያስፈልገዋል፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ የፖለቲካ ዕውቀት፣ ልምድ፣ ሥነ ምግባርና የጋለ ፍላጎት ባላቸው ሰዎች ሊሞላ ይገባል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎችም የአኩራፊዎች መሰባሰቢያ ከመሆን በዘለለ፣ በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት መመሥረት ይኖርባቸዋል፡፡ የፖለቲካው ምኅዳር ከሚችለው በላይ ቁጥር ያላቸው የምርጫ አጃቢ ፓርቲዎች የሚርመሰመሱበት፣ በአብዛኛው ለፖለቲካ ብቁ ያልሆኑ ሰዎች ስለሚበዙባቸው ነው፡፡ በሚገባ ሊረዷቸው የሚችሉ አባላትና ደጋፊዎች ሳይኖሯቸው የሚቋቋሙ ፓርቲዎች የረባ ቢሮ የላቸውም፡፡ ከአባላት መዋጮም ሆነ ከሌሎች ደጋፊዎች የሚገኝ በቂ ፈንድ ስለማይኖራቸው፣ የረባ ፕሮግራም ወይም ማኒፌስቶ ለማዘጋጀት የሚያስችል አቅም አይገነቡም፡፡ ምርጫ ሲካሄድ ከሚያገኙት አነስተኛ የድጎማ በጀት በስተቀር ምንም ስለሌላቸው፣ በምርጫ ቅስቀሳ ጊዜ እዚህ ግባ የሚባል ክርክር ለማድረግ የሚችሉ ተከራካሪዎች ይዘው ስለማይቀርቡ መሳቂያ ይሆናሉ፡፡ ኢትዮጵያ በሚገባ የተጠናከሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያስፈልጓታል፡፡ የኢትዮጵያን ሕዝብ የሚመጥኑ አማራጮችን ይዘው የሚፎካከሩ ጠንካራ ፓርቲዎች ሲኖሩ፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ክብርና ሞገስ ታገኛለች፡፡

የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰብሰብ ብለው በጥንካሬ ለፉክክር የሚሆን አቅም ሲገነቡ፣ የፖለቲካ ምኅዳሩም አሳታፊ ለመሆን የሚያስችል ዕድል ይሰፋለታል፡፡ የሲቪል ማኅበረሰቡም ሆኑ ሌሎች ባለድርሻ አካላት በሕዝቡ ውስጥ የዴሞክራሲ መሠረታዊ ግንዛቤዎችን ከማስረፅ ጀምሮ፣ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ሊኖር የሚገባውን ፍትሐዊ ግንኙነት መልክ እስከ ማስያዝ ድረስ ሚናቸው የጎላ ይሆናል፡፡ ሚዲያዎች ሙያቸውን መሠረት አድርገው ሁሉንም ወገን በገለልተኝነት የማስተናገድ አቅማቸውን ይገነባሉ፡፡ ዜጎች መብትና ግዴታቸውን በሚገባ በመገንዘብ በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ ድጋፋቸውንና ተቃውሞአቸውን መግለጽ ይችላሉ፡፡ የፍትሕና የፀጥታ አካላት በነፃነትና በገለልተኝነት ኃላፊነታቸውን ይወጣሉ፡፡ የመንግሥትም ሆነ የሌላ ወገን ጣልቃ ገብነት የምርጫ ቦርድንም ሆነ የሌሎች ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን ማስጨነቅ አይችልም፡፡ ኢትዮጵያ ከጎረቤቶቿም ሆነ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች አንፃር ያለችበትን አሳዛኝ ዴሞክራሲያዊ ደረጃ በመገንዘብ፣ ይህ ትውልድ ልዩነቶቹን አቻችሎም ሆነ ዕውቅና ተሰጣጥቶ ለመሠረታዊ ለውጥ መነሳት አለበት፡፡ ገዥው ፓርቲ አውራ ሆኖ ሌሎች እየጫጩ የሚሄዱበት ብልሹ አሠራር ይለወጥ፡፡ ጠንካራ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ሲኖሩ ኢትዮጵያም ትኮራለች፡፡

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር የሚረዳ የምክክር ኮሚሽን ተመሥርቶ ሥራ ለመጀመር ዝግጅቱን እያጠናቀቀ ነው፡፡ የኢትዮጵያን የዘመናት ችግሮች ለመፍታት ልማት አንደኛው መንገድ ቢሆንም፣ ህልውናዋን አስቀጥሎ ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ የሚቻለው ተቀምጦ በመነጋገር ነው፡፡ ግራና ቀኝ ተሠልፎ የጦርነት ነጋሪት ከመጎሰም ይልቅ፣ በዚህ ዘመን ጭምር የተፈጠሩ ችግሮችን በመፍታት ወደፊት ለመራመድ ምክክር አስፈላጊ ነው፡፡ በአገር ዙሪያ ገብ ችግሮች ላይ ተቀምጦ ለመነጋገር ደግሞ መከባበር፣ ለልዩነቶች ዕውቅና መሰጣጠትና አገርን ከምንም ነገር በላይ ማስቀደም በትንሹ የሚጠየቁ መሥፈርቶች ናቸው፡፡ በዚህ መሠረት ራስን ማዘጋጀት ሲቻል ሕግ ይከበራል፣ ግጭት ይወገዳል፡፡ የመንግሥትን ልጓም የሚጨብጡም ሆኑ ማንኛውም ዜጋ ከሕግ በታች መሆኑ የሚረጋገጠው፣ በአገር ጉዳይ በእኩልነት ለመነጋገር የሚያስችል ምኅዳር ሲኖር ነው፡፡ አንዳንድ ወገኖች ለአገራዊ ምክክሩ ዝግጅት ድጋፍ ከማድረግ ይልቅ ትችት ላይ ብቻ ሲያተኩሩ ይታያሉ፡፡ ይህ ፈፅሞ ትክክል አይደለም፡፡ ዴሞክራሲ የተሟላ የሚሆነው በጎደለው በጋራ ሲጨምሩበት እንጂ፣ ዳር በመሆን በሚሰነዘር ትችት እንዳልሆነ መታወቅ አለበት፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያን የአፍሪካ ጭራ እንዳናደርጋት እንጠንቀቅ! 

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈውን ዜና በመገረም እየተመለከቱ አገኟቸው]

ምንድነው እንዲህ ቀልብሽን የሳበው? ስለሰላም ኖቤል ሽልማት ዜና እየተመለከትኩ ነበር። እና...

የወሎ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ መመሥረትና የአማራ ክልል ጥያቄ

አማራ የኢሕአዴግ አንዱ መሥራችና አጋር ከሆነው ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ...

የሽንኩርት ዋጋ ሰማይ የነካበት ምክንያት ምንድነው?

ባለፉት ሁለትና ሦስት ሳምንታት የሸማቾችን ኪስ ካስደነገጡ መሠረታዊ ከሚባሉ...

የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ኤግዚቢሽን ማዕከልን እንዲያስተዳድር የተሰጠው ኮንትራት ለምን ተቋረጠ?

በአዲስ አበባ ከተማ ለንግድ ትርዒት ዝግጅት ብቸኛ በመሆን የሚጠቀሰው...

የመከፋት ስሜት!

ከቤላ ወደ ጊዮርጊስ ልንጓዝ ነው፡፡ መውሊድና መስቀልን በተከታታይ ቀናት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

ግጭቶች በሙሉ ሁሉን አሳታፊ መፍትሔ ይፈለግላቸው!

የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ተገቶ የተስፋ ጭላንጭል መታየት ሲጀምር፣ በአማራ ክልል ሌላ ዙር ዕልቂትና ውድመት ሊያደርስ የሚችል ግጭት መነሳቱ ብዙዎችን ያሳስባቸዋል፡፡ በአማራ...

የባለሥልጣናትና የባለሀብቶች ግንኙነት ሥርዓት ይኑረው!

በሕዝብ ድምፅ ሥልጣን የያዘ ፓርቲ የሚመሠርተው መንግሥት ከምንም ነገር በፊት ለሕግና ለሥርዓት መከበር ኃላፊነት ሊኖረው ይገባል፡፡ ይህንን ኃላፊነት በሚገባ ሊወጣ የሚችለው ሥራውን በግልጽነትና በተጠያቂነት...

የመላው ሕዝባችን የአብሮነት ፀጋዎች ይከበሩ!

ሕዝበ ሙስሊሙና ሕዝበ ክርስቲያኑ የመውሊድ፣ የደመራና የመስቀል በዓላትን እያከበሩ ነው፡፡ በኢትዮጵያ አገረ መንግሥት ግንባታ ውስጥ እኩልና ጉልህ ድርሻ ያላቸው ኢትዮጵያውያን፣ በዓላቱን እንደ እምነታቸው ሕግጋት...